Thursday 2 July 2015

የሽሮን ጥጋብ ስለማላቀው እጄን ያዙኝ ያሉ አንድ አባት ነበሩ (በፋጡማ ኑርዬ)

አንድ አባት ነበሩ ፤ ስጋ ቤት አላቸው፤ ስለዚህ ስጋ ነጋዴ ስለሆኑ ብዙ ጊዜ እቤታቸው ውስጥ የሚበላው ስጋ ነው ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሚስታቸው ሽሮ አማረኝ ብለው ሽሮ ሲሰሩ ፤ ቤቱ ውስጥ የተሰራው ሽሮ ብቻ ስለሆነ የግዳቸውን መብላት ይጀምራሉ ፤ እየበሉ በመሀል ልጆች ‹‹የሽሮን ጥጋብ ስለማላቀው ስጠግብ እጄን ያዙኝ››….. ብለው ቤተሰቡን ያስቃሉ፡፡አሁንም ኢህአዴግ የስልጣንን ጥጋብ ስላላወቀው አባገነንነቱን አጠናክሮበት ቀጥሏል፡፡ ሀይ ባይ ያጣም ይመስላል፤ በህዝብ ገንዘብ ስብሰባ እያዘጋጀ ህዝቡን በግብር እያስጨነቀ በሰበሰበው ብር በማን አለብኝነት፤ ህዝቡን ያሸብራል፣ ያስራል ፣ ይገድላል ፣ ከሀገርም ያሳድዳል ፡፡ ይህም አልበቃ ብሎት በየስብሰባው ላይ ፍርድ ቤት ጉዳያቸው እየታየ ያሉትን ወንጀለኝነታቸው በፍርድ ቤቱ ሳይረጋግጥ ህገ መንግስቱን በመጣስ በየአደባባዩ ሚሊዮኖች የወከሏቸውን ወኪሎቻችንን አሸባሪ የሚል ስያሜ እየሰጡ፤ ህዝበ ሙስሊሙን ለማሸማቀቅ እየጣሩ ይገኛሉ፡፡
በአዳማው ቲታስ ሆቴል በተካሄደውና፤ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት፤ ባዘጋጀው ስልጠና ላይ ፤ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስቴር የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴንና በተለይ ምክትላቸው አቶ ሽመልስ ከማል መንግስት አሁንም በእስልምና እምነት ዘልቆ መግባቱ የሚያሳዩ ንግግሮችን አድርገዋል። አቶ ሬድዋን ሁሴን በዋናነት ሽብርተኝነት በተመለከተ በምዕራባውያን እይታና በኢትዮጵያ መንግስት እይታ መካከል ያለውን ልዩነት አብራርተዋል።
ምክትላቸው አቶ ሽመልስ በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት በሀገራችን በእስልምና እምነት ስር ፤ ሰለፊዝም በሚባለው አስተምህሮት አማካኝነት ፤ ወደ ሽብር እየገባች እንደሆነ ያስረዱ ሲሆን በንግግራቸውም <<ሰለፊዝም ባለበት ቦታ ሁሉ ጦርነት አለ፡፡ የሰለፊዝም አስተሳሰብ የሚያራምዱ አካላት ሁሉ ዓለማዊ መንግስት አይቀበሉም፡፡ በሸሪዓዊ ስርዓት ብቻ ነው፡፡ የሚያምኑት የሀገርን ህልውና ያፈራርሳሉ፡፡ ለምሳሌ አይኤስአይኤስ (ISIS) የተባለውም ቡድን ይሄ ነው አላማው ፡፡በሀገራችንም እነዚህ አካላት እራሳቸውን ማጠናከር ጀምረው እስከሚኖሩበት አከባቢም መነጠል ጀምረዋል፡፡ ለምሳሌ ኮልፌና አየር ጤና ይሄንን አስተሳሰብ ልንከላከለው ይገባል፡፡ ከዚህ ቀደም በሀገራችን የነበረው የሱፊዝም እስልምና ተከታዮች ከህብረተሰቡ ጋር አብረው መኖር ይችላሉ። አሁን የዚህ ተከታዮች እየጠፉ ነው፡፡ አስተማሪዎቻቸውም እንዲጠፉ እየተደረገ ይገኛል፡፡ ይሄንን አስተምህሮት ልንደግፈው ይገባል፡፡ ለዚህ ትልቁን ድርሻ እየተወጣ ያለው አንዱ የሰለፊዝም አካል ወሀቢዝም የሚባለው አስተምህሮት ነው። በሀገራችን ከ2004 ጀምሮ የተከሰተው የእምነት ችግር ከዚሁ ጋር ይያያዛል በወቅቱ ለዚህ ተጠያቂዎቹ አሁን በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸውን በፍርድ ቤት እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡ ወሀብዮችና ሰለፊስቶች አንድ ናቸው፡፡ በአካሄድ ብቻ ልዩነት አላቸው፡፡ እነዚህ አካላት ከዚህ በላይ ከተጠናከሩ፤ እንደ ናይጄሪያ ትልቅ ቀውስ ማስከተላቸው አይቀርም፡፡ በገንዘብ አቅም በኩል ጎልበተዋል በቴክኖሎጂም የሚፈልጉትን የሚፈፅሙበት ላይ ይገኛሉ>> በማለት በጥቅሉ መንግስት አሁንም በእስልምና እምነት ላይ ጣልቃ መግባቱን እንደሚቀጥል የሚያረጋግጥ ንግግር አድርገዋል።
ፍተሻ ፡- እንደነ ሽመልስ ከማል አይነቶች የህወሀት ተላላኪ በየሚዲያው እየወጡ የሚያደርጉት እንዲህ አይነቱን ንግግር የህዝበ ሙስሊሙ አቋም ምንድን ነው? ኮሚቴዎቹ እስካሁን በኛ ቁጥጥር ስር ሆነው እንደፈለግን እያሰቃየናቸው ነው ፡፡ ህዝበ ሙስሊሙ እስካሁን የታሰሩት ይፈቱ እያሉ ከመጮህ የበለጠ ምን የተለየ ነገር ያመጡት ነገር የለም፡፡ ብንፈርድስ ምን ያመጣሉ? በየሚዲያው እየወጣን የህዝቡን ስሜት እንፈትሽ ህዝበ ሙስሊሙ ምንም አያመጣም የሚል ንቀት እና ማን አለብኝነት የተሞላ ንግግር ነው፡፡
አሁንም መንግስት ያላወቀው እና ያልተረዳው ነገር ቢኖር ኮሚቴዎቻችን እና ህዝበ ሙስሊሙ እሱ እንደ ሚያስበው ጨቅላ አስተሳሰብ ያላቸው አለመሆኑ ነው፡፡ ህዝበ ሙስሊሙ ሊያውቀው እና ሊረዳው የሚገባው ነገር ቢኖር መንግስት ነን ብለው ከተቀመጡት አባገነኖች በብዙ እጥፍ ኮሚቴዎቻችን በአመለካከትም በማንነትም እንደ ሚበለጡ ነው ፤የሚያሳው ለዚህም ነው ፤ በየአደባባዩ ፍርድ ቤት የያዘውን ጉዳይ እያነሱ አሸባሪ እያሉ ሰሚያጣ ንግግር የሚያደርጉት፡፡
አምስት ሳንቲም ፡- ስዩመ እግዚያብሄር ብለው እራሳቸውን ሰይመው የኢትዮጵያ ህዝብ ለግማሽ ምእተ አመት ህዝቡ በፍርሀት እንደ ፈጣሪ ሲሰገድላቸው የነበሩትን ኃ/ስላሴም እንኳን በአምስት ሳንቲም የዋጋ ጭማሪ ሰበብ የተነሳባቸው ህዝባዊ አመፅ የሚዘነጋ አይደለም ፡፡ ይንም ታሪክ የኢሀአዴግ መሪዎች የሚያቁት ነው፡፡
ደርግም ፡- ከአፍሪካ በወታደራዊ ሀይሉ አንደኛ የተባለለት አምባገነኑ ደርግም አንድ ሰው እና አንድ ጥይት እስከሚቀር ድረስ እንዋጋለን ብሎ ሲፎክር የነበረውም ፤ ህዝቡ በቃህን ሲለው ፍፃሜው ምን እንደ ሆነ የምናቀው ታሪክ ነው፡፡
አሁንም ኢሀአዴግ ሆይ …. የሽሮን ጥጋብ ………… እንዳሉት ተረት የስልጣንን ጥጋብን ያወቀው አይመስልም ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ያነሳልም ይጥላልም ፤ ስለዚህ በብሄር ፣ በዘር ፣ በእምነት ከፋፍዬ አለሁ ብሎ ምንም አያመጡም እንደፈለገን እንጨፈልቃለን የሚለው አስተሳሰባቹሁ የትም እንደማያደርሳችሁ ልታውቁ ይገባል ፡፡ አንደውም ለህዝቡ በጣም የነፃነቱን ቀን እያፈጠናችሁለት እንደሆነ ነው ፤ የሚታመነው በዘር ፣ በብሄር ተከፋፍለው እርስ በርስ መተማመን እና አንድነት የጠፋውን ሁሉ ዛሬ እምነትን መጨቆን እና መድፈር ሲጀመር ግን በዘር እና በብሄር የተለያየው ሁላ ዛሬ ላይ በአንድነት ሰንሰለት የተያይዙበት ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡
አሁንም ኢሀአዴግ እያለን ያለው ነገር ሰሚ አጥቼ ነው እንጂ ‹‹የስልጣንን ጥጋብ አላቀውም እና አንሱኝ ነው››፡፡ ስለዚህ እኛ ደግሞ አንድ ሆነን የስልጣን ጥጋብህ እዚህ ጋር በቃህ ፤ መታሰር መጨቆን መሮናል ሰልችቶናል ፤ ያለምንም ውዝግብ ውረድ …. በአንድነት የኖረን ህዝብ እያወክ እና ሀገሪቷን ታሪክ አልባ እንቅስቃሴ ሊበቃ ይገባል፡፡ ይህ ማድረግ ካልቻልክ ግን የሚፈጠረው ነገር ቀላል አይሆንም ወደ ኋላ መለስ ብሎ የአምስት ሳንቲሟን ታሪክ ማስታውስ ተገቢ ነው፡፡