Thursday 26 May 2016

ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ ምኑ ነው?

(በኤልሳቤጥ ግርማ ከኖርዌይ)
በዚህ በያዝነው ወር በየዓመቱ ስለግንቦት 20 በተለያየ መልኩ ይሰበካል፣ ይገለጻል። ለሀገራችን ኢትዮጵያ ታምራዊ ለውጥ እንዳስመሰገበ ሁሉ ወሩን ሙሉ ሲተረክ መስማት እንደ ሀገራዊ መዝሙር የተለመደ ሆኗል:: በተለይ የሥርዓቱ ባለቤቶችና ደጋፊዎች ምስኪኑን ሕብረትሰብ ሳይቀር በማስገደድ ቀኗን “ልዩ ቀን” “የድል ቀን” “የስኬት ቀን” በማለት ሰይመው በአስረሽ ምችው ሲከበር ማየት ድፍን 25 ዓመታትን አስቆጠረ።
eprdf-tplf
ጀግናው የኢህአዲግ ሰራዊት ደርግ ኢሰፓ ሲጠቀምበት የነበረውን የሬዲዮ ጣቢያ ተቆጣጥሮታል ሺ ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ሦስት ብለው እንዳበሰሩን በእርግጥ ለጥቂቶች ግንቦት 20 የድል ቀን ነው:: ምክንያቱም ሀገሪቱን በአንባገነናዊ አገዛዝ ለማስተዳደርና የስልጣን ጥማታቸውን ለማርካት መሰረት የጣሉባት እና የአስራ ሰባት ዓመት የልፋት ዋጋቸውን ያገኙባት ልዩ ቀን ናትና:: በዚች ቀን ህብረተሰቡን በምስጢራዊ የአገዛዝ ስልት ለማስተዳደርና ስልጣናቸውን ዘላለማዊ ለማድረግ የነበራቸው ሕልም እውን የሆነባት ቀን ናትና በልዩ አከባበር ቢያከብሯት ሲያንሳት እንጂ አይበዛባትም::
የተወሰኑ የስራዓቱ አቀንቃኞችም ስለቀኗ መልካምነትና ከዚያች ቀን በኃላ አገራችን ኢትዮጵያ በልማት ጎዳና የገስገሰች፣ የዜጎች አኩልነት የተረጋገጠባት፣ ፍትህና ዲሞክራሲ የሰፈነባት፣ ሰባዊ መብቶች የተከበሩባት፣ ፍትሃዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ የታየባት፣ ህብረተሰቡን በእኩል የሚያስተዳድር መንግስትና ሕግ መንግስት የተመሰረተባት አገር እንድትሆን ግንቦት 20 ታሪካዊ የድል አሻራ እንደጣለች በኩራት አፋቸውን መልተው ይናገራሉ:: ይባስ ብለው ከውጭ ወራሪ ወይም ቅኝ ግዛት ኢትዮጵያን ነፃ ያወጧት ይመስል ግንቦት 20ን የነፃነት/ሀገራዊ ቀን ለማድርግ የሚሞክሩ ብልጣብልጥ የስራዓቱ ደንገጡሮችም አሉ::
በእርግጥ የደርግ አንባገነን መንግስት የአጼ ኃይለ ስላሴ መንግስትን ገርስሦ በምትኩ ወታደራዊ ጁንታ በመመስረት ስሙን በመቀያየር አገዛዙ ለ17 ዓመታት ኢትዮጵያን በብዙ ዘርፈ ብዙ ችግሮች በተለይ ሀገሪቱን መለወጥ ይችላሉ ተብለው የሚታሰቡትን 60 ሚኒስተሮች በመረሸን፣ ነጭና ቀይ ሽብር በማለት ሀገር ተረካቢ ትውልድን በማስጨፍጨፉ የኢትዮጵያ ህዝብ የደርግን ስርዓት አንቅሮ ተፍቶት ነበር። የለውጥ ያለሽ ብሎ በመጮህ ከደርግ አረመኔያዊ የጭካኔ አገዛዝ ነጻ ሊያወጣው የሚችል መለኮታዊ ኃይል እስኪፈልግ ድረስ የኢትዮጵያ ህዝብ በሙሉ ለውጥ ፈላጊ ሆነ።
ህወሓት የህዝቡን ብሶትና እሮሮ ተጠቅሞ 17 ዓመት ጫካ ውስጥ ያረገዘውን መርዝ ለመርጨት ግንቦት 20 ደርግን ገርስሦ በትረ ስልጣኑን ጨበጠ። እዚህ ላይ ወያኔ የደርግን ስርዓት ሳያይና በትንሹም ቢሆን ለውጥ እንዲመጣ ጥረት ሳያደርግ ለትግል ወደ ጫካ መግባቱ ሀገራዊ ለውጥ አሳስቦት ሳይሆን የብሄር ፖለቲካ ጥማት እንደሆነ በትክክል መገንዘብ ይቻላል፤እያየነውም ነው። የብሄር ፖለቲካ ደግሞ እንደ ኢትዮጵያ በርካታ ብሄር ብሄረሰቦችን ለምታስተናግድ ሀገር ቀርቶ ለየትኛውም የአለም ሀገራት የማይበጅ መሆኑ የታወቀ ነው። ኢትዮጵያም የከፋፍለህ ግዛውና የጎሳ ፖለቲካ እንደማይጠቅማት ከዘመነ መሣፍንት ትምህርት ቀስማ ነበር። ዳሩ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ የደርግን ሥርዓት ጥላቻና ሽሽት ዘረኛው ወያኔን ግንቦት 20 በሩን ከፍቶ እጁን ዘርግቶ ተቀበለ።
ወያኔዎች የደርግን ሥርዓት ገርስሰው መንግስቱ ኃይለ ማርያምን ወደ ዝምባብዌ ካስኮበለሉ በኋላ ሥልጣናቸውን ለማጽናት የይስሙላ ህገ መንግሥት አርቅቀው አጸደቁ። ለተወሰኑ ዓመታትም የነጻነት በርን ለመከፈትና ስላምና መረጋጋትን ለማስፈን የመጡ እስኪመስል ድረስ ሰላምን ሰበኩ። ከደርግ ጋር ንክኪ አላቸው ተብሎ የሚጠረጠሩ ግለሰቦችን በሙሉ እስር ቤት ወረወሯቸው። ከገጠር እስከ ከተማ ህብረተሰቡ ለራሱ መጠበቂያ ብሎ የገዛዉን ትጥቅ ሳይቀር በሙሉ አስፈቱ። የኢትዮጵያ ህዝብ ግንቦት 20 በየዓመቱ “የድል ቀን” እያለ እንዲዘምር ተደረገ።
በእውኑ ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ ምኑ ነው? ይህ ጥያቄ በተለያየ መልኩ በሁላችንም አይዕምሮ ውስጥ እንደሚመላለስ እርግጠኛ ነኝ። መልሳችን ግን በራሳችን ምዕናባዊ እይታ ስለምንመለከተው የተለያየ ሊሆን ይችላል፤ ሆኖም ግን ከሁለት አማራጮች ሊዘል አይችልም። ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ ወያኔዎች እንደሚሉት “የድል ቀን” ወይም ብዙዎች እንደሚስማሙበት “የውድቀት ቀን” መሆን አለበት። ወያኔዎችና ደጋፊዎቻቸው ግንቦት 20ን “የድል ቀን” ማለታቸው በእርግጥም ትክክል ናቸው። ምክንያቱም በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የአንባገነን ስልጣናቸውን ያፀኑበት እና በሦስቱም ዘርፍ ማለትም ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮችን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠሩበት ቀን ነውና።
እውነታው ሲገለጥ ግን ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ የውድቀት እና የውርደት ቀን እንጂ በምንም መመዘኛ የድል ቀን ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም ለአንድ ሀገር የድል ቀን ሲባል ዜጎቿ እኩል ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችል በጎ አጋጣሚ ወይም የኩራት ምንጪ ሲፈጠር ብቻ ነው። ግንቦት 20 ግን ከዚህ በተቃራኒው መሆኑን ግልጽ ሊያደርግ የሚችል ብዙ ማሳያዎች ከመኖሩም ባሻገር በኢትዮጵያና በህዝቦቿ ላይ የደረሰውንና እየደረሰ ያለውን ችግር ዘርዝሮ መናገር ይቻላል።
“የድል ቀን ሆይ የት ነሽ?ምንጭሽስ ከቶ ከወደየት ይገኛል?”
የኢትዮጵያ ህዝብ ከግንቦት 20 የተቀበላቸውን ገጸ እርግማኖች ለማሳያ ያክል እንደሚከተለው እናያለን፤
የብሄር ፖለቲካ የተፀነሰበት
የህወሓት ማፍያ ቡድን ገና ከጅምሩ ሃገራዊ ፍቅር ሰንቆ እንዳልመጣ ከስሙ መረዳት ይቻላል። የትግራይ ነጻ አውጪ ቡድን ብሎ መሰየሙ ለኢትዮጵያና ለህዝቧ እንዳልቆመ ለመረዳት ነብይነት አያሻውም ነበር። የከፋፍለህ ግዛው መርህን በማንፌስቶው ይፋ አድርጎ ይንቀሳቀስ እንደነበር ሰነዶች ህያው ማስረጃ ናቸው። ለስልጣን ማራዘሚያ በዋናነት የተጠቀመበት ዋናና ትልቁ አጀንዳ የብሄር ፖለቲካን ነው። ምክንያቱም የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ካልሆነ በስተቀር ከስልጣን ሊወርድ የሚችልበት ምንም አይነት አጋጣሚ እንደሌለ በሚገባ ያውቃልና። የብሄር ፖለቲካ እያራመደ እርስበርሳችን እንዳንተማመን በብሄር ለያይቶናል። ይሄ የናንተ መሬት ነው፣ ይህ ደግሞ የነሱ ነው ወዘተ እያለ በቡድን ከፋፍሎናል። በብሄሮች መካከል መግባባት እንዳይኖር እነእገሌ እንዲህ አደረጓቹህ፣ ታሪካችሁ እንዲህ ነው በማለት መጀመርያ መምጣት ያለበት ብሄር ነው ወዘተ እያለ የብሄር ጥላቻ እንዲሰፍን ሀውልት ሰርቶልናል። አንድ ዜጋ ኢትዮጵያዊ ነኝ ከማለት ይልቅ በውሸት የብሄር እኩልነት ስም ኦሮሞ፣አማራ፣ ጉራጌ፣ አፋር፣ ሶማሌ፣ ጋምቤላ እያለ በየቦታው እራሱን እያዋረደ እርስ በእርሳችን በጥላቻ እንድንናቆር ማድረጉ የወያኔ የብሄር ፖለቲካ ውጤት ነው። ስለዚህም ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ የድል ቀን ሳይሆን የብሄር ፖለቲካ የተፀነሰበት የውርደት ቀን ነው። “የድል ቀን ሆይ የት ነሽ?ምንጭሽስ ከቶ ከወደየት ይገኛል?”
ትውልድ ገዳይ ሥርዓተ ትምህርት የተቀረጸበት
ትምህርት ቤቶች ለአንድ ሀገር ተተኪ ዜጋ ፈጣሪ ተቋም እንደመሆናቸው መጠን የሃገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ፣ ታሪክንና ባህልን ከማሳወቅ ባለፈም በማንነት ላይ የተመሰረተ ጥራት ያለው ዜጋ ለማፍራት የሚቀረጸው ሥራተ ትምህርት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል። ነገር ግን ወያኔ የቀረጸው ሥርዓተ ትምህርት ግን ትውልድን ገዳይና የተማሪዎችን አይዕምሮ ለምርምርና ጥናት የማይጋብዝ ዘላቂና አስተማማኝ ያልሆነ ጥራት የጎደለው ሥርዓተ ትምህርት ነው። ትምህርት ቤቶችም ተማሪዎችን በጥሩ ሥነ ምግባርና ባህልን ከማሳዎቅ አንጻር አስተምሯቸው ዝቅተኛና ከዚህ ግባ የማይባል መሆኑ ለትውልዱ መጥፋት ሌላው የወያኔ የስርዓቱ ውጤት ነው። ትምህርት ቤቶችን ስንመለከት ከተቀረጸላቸው ሥርዓተ ት/ት ጀምሮ ትውልድን ለመቅረጽ ቀርቶ በዜግነት ደረጃም እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ የሚናገር ትውልድ እንዲጠፋ በማድረግ ረገድ ግንቦት 20 የራሷን ጥቁር ጠባሳ ጥላለች። አንዳንድ የዘመነ ወያኔ ተማሪዎች የሀገረን ታሪክ በሚገባ ካለማዎቅ የተነሳ ቅኝ ግዛት በተገዛን ኑሮ ሲሉ መስማት የሥርዓተ ትምህርት ውድቀቱን ማሳያ አንዱ መንገድ ነው።
የሃገር ዳር ድንበር የተደፈረበት
አንድ ሀገር የድል ቀን የምታከብር ከሆነ ለሀገርና ለህዝብ የሚቆረቆር መንግሥት አላት ማለት ነው። መንግሥት ካለ ደግሞ የሃገር ሉዓላዊነት ተጠብቆ፣ ታሪኳ ሳይበረዝና ሳይፋለስ ለትውልድ መተላለፍ ይችላል ማለት ነው። ወያኔ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ግን የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ ዳር ድንበሯ የተደፈረባት፣ ወደቧን ያጣችበትና ታሪኳ የተበረዘበት ዘመን ነው። ድሮ አባቶቻችን ቅኝ አንገዛም በማለት ታሪካችንና ባህላችን ሊበረዝ ከቶ አይችልም ብለው አጥንታቸውን ከስክሰው፣ ደማቸውን አፍስሰው፣ ውድ ህይወታቸውን ሰውተው ዳር ድንበሯን ከነሙሉ ክብሯ ያቆዩልንን ሀገር ወያኔ ለአረብና ህንድ ባለሃብቶች ማቀራመቱ ሳያንሰው ሱዳን የድርሻሽን ውሰጅ ብለው በመማጸን ላይ እንደሆኑ ስንሰማ በእውነትም ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ የውርደትና የውድቀት ቀን ነው። ዜጎቿ በሄዱበት ሞትና እንግልቱ ሳያንሳቸው በእራሳቸው ሀገር በሌላ ዜጋ እንደ እንስሳ ደማቸው ሲፈስና ህጻናት በገፍ ተግዘው ሲሄዱ ከማየት በላይ ምን የተለየ ውርደትና ውድቀት ይኖራል። “የድል ቀን ሆይ የት ነሽ?ምንጭሽስ ከቶ ከወደየት ይገኛል?”
ህዝቦቿ ለሞት፣ለስርና በስደት ለውርደት የተዳረጉበት
በወያኔ አገዛዝ ከ1983 እንደ ኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር ከግንቦት ወር ጀምረን በግፍ ውድ ህይወታቸውን በስውርና በአደባባይ የተቀሰፉ፣ ለስር፣ ለእንግልትና ለስደት የተዳረጉ ዜጎችን የሰማይ አምላክ ይቁጠራቸው እንጂ በአኃዝ ማስቀመጥ እጅጉን ይዘገንናል። ተፈጥሯዊና ሰባዊ መብቶች በይፋ ተገርስሰዋል። የስርዓቱ አባል፣ ደጋፊና አገልጋይ ካልሆነ በስተቀር በሀገሩ ምድር ቀና ብሎ የመናገር፣ የመጻፍ፣ የመደራጀት እና የመስራት መብቶች ፈጽመው መገደባቸው የአደባባይ ምስጢር ነው። ወያኔዎች ግንቦት 20ን የድል ቀን ብለው ማክበር ከጀመሩ ጀምሮ በሀገሪቱ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የግፍ ጽዋ ሞልቶ ፈሷል። ህዝቦቿ በሄዱበት ሁሉ የውርደት ካባ እየተከናነቡ ተቆርቋሪ ያጣ ዜጋ በመሆኑ ዋይታና ልቅሶው ከመቸውም በላይ ጨምሯል። “የድል ቀን ሆይ የት ነሽ?ምንጭሽስ ከቶ ከወደየት ይገኛል?”
በአጠቃላይ ኢትዮጵያ አገራችን የተለያየ መልክና መገለጫ ያላቸው በርካታ መንግሥታትን ያስተናገደች አገር ብትሆንም ለዘመናት ታሪኳን፣ ባህሏን፣ እምነቷን፣ አንድነቷን፣ ድል አድራጊነትን እና ዳር ድንበሯን ጠብቃ አስጠብቃ የኖረች እና መተሳሰብን፣ መከባበርን፣ እንግዳ ተቀባይነትን፣ ዘርንና ጎሳን መሰረት ሳታደርግ ለዘመናት የቆየች የጀግኖች አገር ነበረች። ነገር ግን ግንቦት 20 የለገሰን የአሳርና የግፍ ፍሬዎች በቀላሉ የማይሽሩ እኩይ ተግባር ናቸውና ታሪካዊ አገራችንን አደጋ ላይ ጥሏታል። ስለሆም ጊዜ ሳንሰጥ “የድል ቀን” የሚለውን ተረት ተረት ወደ ጎን በመተው በአንድነትና በህብረት ዛሬውኑ የውርደትን ቀን ወደ የድልና የክብር ቀን ሊቀየር ይገባል። ግንቦት 20 ለኢትዮጵያ ህዝብ የድል ቀን ሳይሆን የሞት፣የውድቀትና የውርደት ቀን ተብሎ ይስተካከል!ምነው ሽዋ! ድንቄም የድል ቀን…………

16 የግንቦት 20 ፍሬዎች!

  • 350
     
    Share
TTPLF
  1. በዐፄ ሠርፀ ድንግል ዘመን ቱርኮች ሀገራችንን ቅኝ ለማድረግ በማሰብ ባሕረ ነጋሽ ይስሐቅን (አሁን ላይ ጥሊያኖች ኤርትራ ያሏት የባሕረ ምድርን ገዥ) በመደለል በገዛ ሀገሩና ሕዝቡ ላይ ክህደት በመፈጸም የሚገዛውን የሀገራችንን ክፍል ይዞ እንዲከዳ በማድረግ ተጀምሮ የነበረው ነገር ግን ወዲያውኑ 1571ዓ.ም. ዐፄ ሠርፀ ድንግል ወደቦታው ዘምተው የከሐዲውን የባሕረ ነጋሽ የይስሐቅንና የወራሪውን የቱርክን ጦር በመደምሰስ ከሽፎ የነበረው፤ በኋላ እንደገና ከአራት ምዕት ዓመታት በኋላ በፋሺስት ጣሊያን ወረራ ለ50 ዓመታት ተነጥሎ የነበረውና ፋሽስት ለቆ መውጣቱን ተከትሎ በተደረገው ዲፕሎማሲያዊ (የአቅንኦተ ግንኙነት) ጥረት እንደገና ወደ እናት ሀገሯ እንድትቀላቀል በማድረግ እንደገና ከሽፎ የነበረው ለበርካታ ምዕት ዓመታት የተደረገው ሀገራችንን ገንጥሎ የመውሰድ የጠላት ሀገራት ጥረትና እንቅስቃሴ በዚያ ምድር ላይ የእነኝህን ጠላት ሀገራት ዓላማ ግብና አቅድ የሚደግፉ የሚያስፈጽሙ የባሪያ ሥነልቡናና ሰብእና ያላቸው የእፉኝት ልጆችን በማፍራቱ እነኝሁ ዜጎች የሚባሉት የገዛ ሀገራቸውን የማፈራረስ ዓላማ አንግበው በመነሣት አሁን ለጊዜው ተደጋጋሚ ሙከራ ሲደረግባት የነበረችውን ባሕረምድር (በባርነት ስሟ ኤርትራን) የገነጠሉና ያስገነጠሉ ገንጣይና አስገንጣይ የጥፋት ኃይሎችን ያገኘንበት፡፡
  2. ዜጎች በዘር በሃይማኖት እንዲከፋፈሉ በመደረጉ የነበረ ፍቅራቸው፣ ትስስራቸው፣ መተማመናቸው፣ ሰላማቸው፣ አንድነታቸው እንዲጠፋ ተደርጎ በጠላትነት እንዲፈላለጉ በጥርጣሬ እንዲተያዩ ሲደረግ ያየንበት፡፡
  3. ግንቦት 20 ያነገሣቸው የጥፋት ኃይሎች መጥተው ከማየታችን በፊት ሊኖሩ ይችላሉ ተብሎ በፍጹም በማይገመት መልኩ “ሰው እንዲህ ሆኖ ይፈጠራል?” በሚያስብል ደረጃ ጠባብ፣ ግፈኛ፣ አርቆና አስፍቶ ማየት ማሰብ የተሳናቸው፣ የማሳስተውሉ፣ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” ባይ፣ ፈጽሞ ኃላፊነት የማይሰማቸውን የነውረኛ የጉድ ፍጥረቶች መንጋ ሀገረ እግዚአብሔር በምትባል ኢትዮጵያ መኖራቸውን ዓይተን ያረጋገጥንበት፡፡
  4. በ20/21ኛው መ/ክ/ዘ በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ ዜጎች የአንድ ብሔር ተወላጆች በመሆናቸው ብቻ ለተለያየ ዓይነት ዘግናኝ የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ሲዳረጉ ያየንበት፡፡
  5. ለሽዎች ዓመታት የኖረች ሀገር ያካበተችው ያቆየችው የኖረችው ያለፈችበት ታሪክ፣ ቅርስ፣ እሴት፣ ማንነት ተቀብሮና እንዲጠፋ ተደርጎ በቦታው ለጥፋት ኃይሎቹ የጥፋት ሥራዎች የሚረዱ ሐሰተኛና የፈጠራ የጥፋት ታሪኮች ሀገር ስትሞላ ያየንበት፡፡
  6. “ከምን ጋር የዋለች ጊደር ምን ተምራ ትመጣለች” እንደተባለው በአብዛኛው ቅን፣ ቅዱስ፣ ጨዋ፣ ታማኝ፣ ደግ፣ አዛኝ፣ ተሳሳቢ ከነበረው ሕዝባችን ቀላል የማይባለው ቁጥር ሳይወድ በግዱ ከእነኝህ ጉዶች ክህደትን፣ እብለትን፣ ሐሰትን፣ ሆድ አምላኪነትን፣ ሸፍጥን፣ ማስመሰልን፣ ቀማኛነትን፣ ስግብግብነትን፣ ኅሊናቢስነትን፣ ነውረኛነትን ወዘተረፈ. ተምሮ ሲረክስ ሲባልግ ያየንበት፡፡
  7. ቀደም ሲል ከነበረው በተናጠል ይፈጸም የነበረው ከዝምድናና ከትውውቅ የሥራ ቅጥር፣ ከሙክትና በእጅ የመጨባበጥ ሰላምታ ከምትሰጥ ጥቂት ብር ጉቦና የሙስና አሠራር ወደ መቶ ሚሊዮኖችና ቢሊዮኖች (አእላፋትና ብልፎች) በግልና በቡድን ከሚዘረፍ የሀገር ገንዘብ ዘርን መሠረት ያደረገ የሥራ ቅጥርና የሙስና አሠራ ከመንኮራኩር በፈጠነ ፍጥነት ተወንጭፎ ሲያድግ ያየንበት፡፡
  8. ለመሠረተ ልማት ግንባታ ስም የሚመጣው ብድርና እርዳታ በጥቂቱ እጅ የወረደ የጥራት ደረጃ ያለው ብላሽ ሥራ ተሠርቶ አብዛኛው በብድርና እርዳታ የመጣ የሕዝብ ገንዘብ እየተዘረፈ እየተበላ ግለሰቦችና ቡድን ሲበለጽጉበት ሰማይ ሲተኮሱበት ሀገርና ሕዝብ ለድርብርብ ጉዳትና ኪሳራ ተዳርገው በትውልደ ትውልድ ተከፍሎ ከማያልቅ የዕዳ ማጥ ውስጥ ሲጠልቁ ሲሰምጡ ያየንበት፡፡
  9. የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀገሪቱ የጥቂቶች በመደረጓና እሱ መተፋቱን ዓይቶ በሀገሩ ተስፋ ከማጣቱና ከመቁረጡ የተነሣ ሀገሪቱን ጥሎ የትም ቢሆን ለመሰደድ የሌት ከቀን ሕልሙ የሆነበትና እየተሰደደም ለበረሀ አውሬ፣ ለባሕር ዓሣና ለአሕዛብ ካራ እንደተዳረገ ዕያየ ያላንዳች መደናገጥና ማቅማማት አሁንም ለመሰደድ ሲገደድ ያየንበት፡፡
  10. ዜጎች ኢትዮጵያዊያን በመሆናቸው ብቻ ስደት በየሔዱበት ሀገራት የሚዋረዱበት፣ የሚታሰሩበት፣ የሚገደሉበት፣ ኩራትና ክብር የነበረው ኢትዮጵያዊነት እርግማን ሆኖ በዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ፊት ብሔራዊ ውርደት ተከናንበን ተሸክመን ስንቀመጥ ያየንበት፡፡
  11. እንደ ሰባዎቹ (1961-1970ዓ.ም.) ዘመናት ወጣቶች ትውልዱ ጠያቂ ሞጋች ተቆርቋሪ አፋጣጭ፣ ሞትንም እንኳ ሳይፈራ የዜግነት ኃላፊነቱንና ግዴታውን ለመወጣት የሚተጋ ሆኖ ሥልጣናቸውና ደኅንነታቸው ችግር ላይ እንዳይወድቅ በማሰብ ትውልዱን ለማፍዘዝ ለማደነዝ በተሠራው ሥራ ትውልዱ በደረሰበት የቅስም (የሞራል) ልሽቀት ስብራት ድቀት ውድቀት የተነሣ ነፍዞና ደንዝዞ ድሮ ድሮ የድሩየነት የወሮበላነት የከንቱነት መለያ የነበረው ጫት ቃሚነትና ሱሰኝነት የዱርየነት መለያ ከመሆን ወጥቶ የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎችና መምህራን መለያ ሲሆን ያየንበት፤ አሁን አሁን ደግሞ በየቢሮው (በየመሥሪያ ቤቱ) በግላጭ ሲያመነዥኩትና ሲጠቀሙት ያየንበት፡፡
  12. የትምህርት ጥራት ድራሹ ጠፍቶ እንኳን ሌላ ስማቸውን እንኳ አስተካክለው የማይጽፉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመራቂዎችን ያየንበት፡፡
  13. በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ኃላፊነቱንና ግዴታውን የማያውቅ፣ የሀገር ፍቅር ስሜቱ የሞተ፣ ለማንነቱ ለክብሩ ለኩራቱ ክብርና ዋጋ የማይሰጥ፣ ከሆዱ በቀር ምንም የሚያሳስበው የሌለው፣ ለሆዱ ሲል ሀገሩን እናቱን ሌላው ቀርቶ “እኔ ከሌለሁ መቸ ልበላው ነው?” ብሎ እንኳ ሳያስብ ራሱንም የሚሸት ትውልድ ፈርቶ ያያንበት፡፡
  14. የኑሮ ውድነት ጣራ ነክቶ ሀብታም፣ መሀከለኛ፣ ድሀ የሚባል የነበረው የዜጎች የኑሮ ደረጃ ፈርሶ ማዕከላዊውን አጥፍቶ በጣም ጥቂት የናጠጡ ሀብታሞችን ጥቂት ድሆችንና እጅግ በጣም ብዙ የድሀ ድሀዎችን በመፍጠር የኑሮ ደረጃዎች ሲዛቡ ያየንበት፡፡
  15. የሀገሪቱ ቅርስና ባለውለታ የሆነችው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋ፣ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋ፣ ክብሯ፣ መታፈሯ፣ መፈራቷ ተጥሶ ተድሶና ተገርስሶ የምናምንቴዎች መጫወቻና መቀለጃ ስትሆን ያየንበት፣ ምናምንቴዎቹም “እንዳታንሰራራ አድርገን አከርካሪዋን ሰብረናል!” ብለው ሲፎክሩ የሰማንበት፡፡
  16. ኧረ የግንቦት 20 ፍሬ ስንቱ ተወርቶ ይዘለቃል? እናንተን ሥራ ማስፈታት ይሆናል እንጅ ዓመት ቢወራ ያልቃል እንዴ! ባጠቃላይ ግንቦት 20 ኢትዮጵያ የጨለማ ዘመኗን ሀ ብላ የጀመረችበት፣ ሕዝብ ሀገሩን የተቀማበትና በገዛ ሀገሩ በቀየው በመንደሩ ግፍ ሰቆቃ የሚቆጥርበት የሚጋትበትን፣ ኢትዮጵያ እንደ ሀገር የወደቀችበት ሕዝቧ እንደ ሕዝብ የተዋረደበትን የአጋንንት መንጋና ዘመን ያገኘንበት ዕለት ነው ግንቦት 20፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ፈጥኖ ከእንቅልፋችን ቀስቅሶ ማቃችንን አውልቀን እንድንጥል ያስችለና!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!! ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

በሐረርጌ የተቀሰቀሰው የተማሪዎች አመጽ ወደ ሌሎች ቦታዎች ተዳረሰ (የፍኖተ ዴሞክራሲ ራድዮ አጫጭር ዜናዎች)

 በተመድ ስር የሚሰሩ ወታደሮች ደሞዛቸው በወያኔ ባለስልጣናት እንደሚበዘበዝ ተጋለጠ
 ስደተኞች ለመቆጣጠር የተቋቋመው የአውሮፓ ህብረት ግብረኃይል የሊቢያን ጠረፍ ጠባቂዎች
እንዲያሰለጥን መመሪያ ተሰጥተው
 በኬኒያ ኩሱሙ በምትባለው ከተማ የተቃውሞ ኃይሎች ያካሄዱትን ሰላማዊ ሰልፍ ለማፈን
ፖሊሶች በወሰዱት እርምጃ ቢያንስ አንድ ሰው ተገደለ
 በዳርፉር መስጊድ ውስጥ የነበሩ ስምንት ሰዎች በአረብ ሚሊሺያዎች ተገደሉ
13254093_10102296231320823_8172214177964234618_n
ዝርዝር ዜናዎች
 ለሳምንታት ጋብ ብሎ የነበረው የተማሪዎች ተቃውሞና የሕዝብ እንድቅስቃሴ እንደገና መቀስቀስ
መጀመሩ ታወቀ። በሐረጌ በዓለማያ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ያገረሽው የተማሪዎች ተቃውሞ እንቅስቃሴ
ለማፈን የወያኔ አግአዚ ጦርና የፌዴራል ፖሊስ ወደ ዩነቨርስቲው ግቢ ውስጥ በመግባት
የተማሪዎችን የመኝታ ክፍሎች ከቀላል መፈንከት እስከ አጥንት ስብራት የደረሰ ድብደባ
መፈጸማችው የሚታወቅ ሲሆን በዚህ የጭካኔ ድብደባ ምክንያት ተቃውሞና ሕዝባዊ ንቅናቄው
በሌሎች የኒቨርሲቲዎናች ከተሞች የተዛመተ መሆኑ ይነገራል። በወለጋ በነቅምት ዩኒቨርሲት
ተማሪዎች ተቃውሟቸውን እንደገና ማሰማት የጀመሩ ሲሆን ወያኔም እንደተለመደው ነፍሰ ገዳይ
አግአዚ ወታደሮችን አሰማርቷል። የሆሩ ጉድሩና የከምቦልቻ ከተማ ነዋሪዎችም ዳግም የመብት
ጥያቄን አንግበው አደባባይ መውጣት ጀምረዋል።
 የወያኔ አገዛዝ ዓለም አቀፍ አስዳሪዎቹን ለማስደሰትና እግረ መንገዱንም ጠቀም ያለ ገንዘብ
ለመሰብሰብ በማሰብ በተመድ ስር በሺህ የሚቆጠሩ ወታድሮች ያሰማራ መሆኑ ይታወቃል። ተመድ
ከፍተኛ የሆነ ደምዝ ለወታደሮቹ በየጊዜው ቢከፈልም የወያኔ የጦር አለቆች ገንዘቡን በመረከብ
ወታደሮችን እየበዘበዙ መሆናቸው ታውቋል። ወታደሮቹ የሞት አደጋ ሲደርስባቸው በግልጽና በይፋ
የማይነገር ሲሆን የተመድ የህይወት ካሳ ክፍያንም ባለስልጣኖቹ እንደሚቀራመቱት ይታወቃል።
ተመድ ባለፈው ሳምንት የተመድ የሰላም አስከባሪዎች ቀንን ምክንያት በማድረግ በተመድ ተልእኮ
ስር ሆነ የተገደሉ ስምንት የወያኔ ወታደሮችን የሸለመ ሲሆን የተለያዩ አገሮች ዜጎች የሆነ 128
ወታደሮቹን ተልእኮውን በመፈጸም ህይወታቸው በማለፉ ክብርና ሚዳሊያ ሰጥቷል።
 በኬኒያ ምዕራባዊ ግዛት በምትገኘው ኩሱሙ በምትባለው ከተማ የተቃዋሚ ኃይሎች ደጋፊዎች
ትዕንተ ሕዝብ ያካሄዱ ሲሆን ከፖሊሶች ጋር በተካሄደው ግጭት ቢያንስ አንድ ሰው የሞተ መሆኑን
የዜና ምንጮች ዘግበዋል። ሟቹ የተገደለው ከፖሊሶች በተተኮሰ ጥይት ነው የሚለውን ዜና የፖሊሱ
ክፍል አስተባብሎ ግለሰቡ ወድቆ መሞቱን ገልጿል። ባለፈው ሳምንት በኬኒያ ዋና ከተማ
በተደረገው የተቃውሞ ስልፍ ፖሊሶች ሰልፉን ለመበተን የኃይል እርምጃ መውሰዳቸው ይታወሳል።
በኩሱሙ የተደረገው ስልፍ የተቃዋሚ ፓርቲዎች የምርጫ ኮሚሽኑን የአድልዎና ብልሹ አሰራር
በመቃወም በተከታታይ ካደረጓቸው ስለፎች ውስጥ አራተኛ መሆኑ ነው።
 የአውሮፓው ኅብረት ሰኞ ግንቦት 15 ቀን ባደረገው ስብሰባ ስደተኞች የሚዲትራኒያን ባህር
አቋርጠው ወደ አውሮፓ እንዳይዘለቁ ለመከላከል የተቋቋመው የባህር ኃይል ግብረ ኃይል የሊቢያ
ጠረፍ ጠባቂዎችን በማሰልጠን ተግባር ላይ እንዲሰማራ ተጨማሪ ኃይላፊነት የሰጠው መሆኑ
ተገልጿል። አፕሬሽን ሶፊያ በመባል የሚታወቀው ይኸው ግብረኃይል በሚቀጥለው ሐምሌ ወር
ውስጥ ኃይላፊነቱ የሚያበቃ መሆኑ የታወቀ ሲሆን በብራስል የተሰበቡት 28 የአውሮፓ አገሮች
የግብረኃይሉን እድሜ ለአንድ ዓመት እንዲራዘም አድርገዋል። ግብረኃይሉ ከተቋቋመ ጀምሮ
ያስገኘው ውጤት አነስተኛ ነው በሚል በተደጋጋሚ ወቀሳ የቀረበበት ሲሆን ኃይሉ እንዲጠናከርና
በማሰልጠን ተግባር ላይ እንዲሰማራ የተወሰነው ድክመቱን አርሞ ውጤት እንዲያስገኝ ነው
ተብሏል።
 በዳርፉር የአረብ ሚሊሺያ አባሎች በአንድ መስጊድ ውስጥ በተሰበሰቡ ሰዎች ላይ በወሰዱት ጥቃት
ቢያንስ ስምንት ሰዎች መገደላቸው ታውቋል። ቀደም ብሎ በአንድ የገበያ ቦታ አንድ የአረብ
ብሔረሰብ አባል የሆነና አንድ የመሳሊት ማህብረሰብ አባል የግል አለመግባባት ፈጥረው በተደጋጋሚ
በዱላ የተመታው መሳሊት አረቡን በስለት ገድሎት እንደነበር ከቦታው የተገኘው ዜና ይገልጻል።
የአረቡ ሚሊሺያ አባሎች ለአረቡ መገደል በወሰዱት የበቀል እርምጃና በአካሄዱት የእሩምታ ተኩስ
በመስጊድ ውስጥ የተሰበሰቡ ስምንት ነዋሪዎችን መግደላቸውንና ከእነዚህ ውስጥ ሁለቱ ልጆች
መሆናቸውን የዜና ምንጮች ገልጸዋል።
 በደቡብ አፍሪካ በፕሬቶሪያ ከተማ ሰሜናዊ ክፍል በህገ ወጥ መንገድ የተሰሩ ቤቶችን ለማፍረስ
የጸጥታ ኃይሎች የወሰዱትን እርምጃ በመቃወም ነዋሪዎቹ የተቃውሞ እንቅስቅስቃሴ
ማድረጋቸውን ከስፍራው የተገኘ ዜና ያስረዳል። ሰኞ ግንቦት 15 ቀን በነበረው ግጭት ቤቶች
ለማፍረስ ከተላከው የአፍራሽ ግብረኃይል አባላት ውስጥ ቢያንስ ሁለቱ መገደላችውን የደቡብ
አፍሪካ ባለስልጣኖች ገልጸዋል። ባለስልጣኖቹ ሃማንስክራል በሚባለው የከተማው አካባቢ በሺ
የሚቆጠሩ ሰዎች በህገ ወጥ መንገድ የሚኖሩ መሆናቸውን ጠቁመው ቦታውን ለማጽዳት ከፍርድ
ቤት ፈቃድ የተሰጣቸው መሆኑን ገልጸዋል።

ጋዜጠኛው አበበ ገላው ያደረገውን በፌስቡክ ጠቅሰህ ሕዝብን ለማነሳሳት ተጥቅመህበታል በሚል በሽብር ተከሰሰ


  • 609
     
    Share
Negere-Ethiopia-edtor-Getachew-Assefa-300x200.jpg
(ዘ-ሐበሻ) የኦሮሚያ ተማሪዎች አመጽ በተቀጣጠለበት ሰሞን መንግስት አስሮ ለረዥም ጊዜ ክስ ሳይመሰርትበት የቆየው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ጋዜጠኛ አበበ ገላው ያደረገውን አድንቀህ ሕዝብን ለማነሳሳት ተጠቅመህበታል እና ከኢሳት ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም ጋር በፌስቡክ እና በስልክ አውርተሃል በሚል የሽብርተኝነት ክስ ቀረበበት::
እንደ ክሱ ዝርዝር ከሆነ
“ተከሳሽ (ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው) በሚጠቀምበት ማህበራዊ ድህረገአጽ በተለይም ፌስቡክ አድራሻው ተጠቅሞ በውጭ ሃገር የሚገኝ የሽብር ቡድኑ አመራር እና አባል ከሆነው አበበ ገላው በልደታ ከፍተኛ ፍ/ቤት በጸረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ተከሶ በመዝገብ ቁጥር 112546 የጥፋተኝነት ውሳኔ ከተሰጠው ጋር ግንኙነት በመፍጠር በቀን 01/9/2006 ዓ.ም በአቶ መለስ ላይ ያደረገው ተቃውሞ መስቀል አደባባይ ላይ ከሚደረግ አንድ ሚሊዮን ሕዝብ የተሳተፈበት የተቃውሞ ሰልፍ የማይተናነስ ነበር:: አሁንም እንዲሁ ኦባማ ላይ ደግሞታል:: የአቤ ጩኸት ዝም ብሎ ያለመገዛት አንድ ድምጽ ብትሆን ለውጥ እንደምታመጣ በጽኑ የማመን ለውጥ አይመጣም ብሎ በተስፋ መቁረጥ ከመቀመጥ የራስን አስተዋጽኦ ማድረግ የተግባር ሰው መሆን ነው በማለት ከሽብር ቡድኑ አባል ጋር የአመጽ ጥሪ በማስተላለፉ”
የሽብር ክስ ተመስርቶበታል 

ዛሬም በቦሌ ክፍለከተማ ወራ ጋኑ አካባቢ 2 ሰዎች በፌደራል ፖሊስ ተገደሉ * በርካታ ሰዎች የደረሱበት ጠፋ

Filed under: News Feature,የዕለቱ ዜናዎች | 
  • 972
     
    Share
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች በአደባባይ እንዲሁም ፌደራል ፖሊሶች አካባቢውን ወረውት)
(ዘ-ሐበሻ) በአዲስ አበባ ከተማ በቦሌ ክፍለ ከተማ ስር ባለው ወራ ጋኑ በተባለው አካባቢ የመንግስት ሃይሎች የአካባቢውን ነዋሪዎችን መኖሪያ ቤቶች በማፍረስ ለሃብታሞች መሬቱን እየቸበቸቡት ሲሆን ዛሬም ቤቶቹን ለማፍረስ ከሄደው ግብረሃይል ጋር የነበረው ፌደራል ፖሊስ 2 ሰዎችን መግደሉን የአካባቢው ሰዎች አስታወቁ::
ከስፍራው የሚመጡ መረጃዎች እንደጠቆሙት በዚሁ አካባቢ ሰሞኑን መሬቱን ለባለሃብቶች መሸጡን ተከትሎ ከ6 ሺህ የማያንሱ ቤቶች ህገወጥ ናቸው በሚል ፈርሰዋል::
ፌደራል ፖሊስ ባለፈው ሳምንት እንዲሁ በዚሁ አካባቢ ቤቶችን ሲያፈርስ በህዝቡ ተቃውሞ ሲደርስበት ከ10 በላይ ሰዎችን መግደሉን ዘ-ሐበሻ መዘገቧ የማይዘነጋ ሲሆን ዛሬም ድርጊቱን የተቃወሙና የት ሄደን እንኑር ያሉ ወገኖች ከመደብደባቸውም በተጨማሪ 2ቱ ሲገደሉ ከ20 በላይ ሰዎችም ታፍነው መወሰዳቸውና የት እንደደረሱ እንደማይታወቅ የአካባቢው ሰዎች ገልጸዋል::

መንገዱን ጨርቅ ያድርግላችሁ ብሎ ሞተ (ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም)

መስፍን ወልደ ማርያም
መንገዱን ጨርቅ ያድርግላችሁ፣ ይቅናችሁ ማለት ነው፤ ለልማት ለሚሰማሩ ሰዎች ምርቃት ይሆናል፤ ለጥፋት ለሚሰማሩ ሰዎች እርግማን ነው፤ እርግማን ብቻም አይደለም፤ የጥፋት ምኞትም ነው፤ ሰዎች ለጦርነት ሲዘጋጁ፣ ሰዎች ሌሎች ሰዎችን ለመግደል ሲሰናዱ፣ ሰዎች እርስበርሳቸው ለመገዳደል ጦራቸውን ሲስሉ መንገዱን ጨርቅ ያድርግላችሁ ማለት ከጀግና አንደበት የሚወጣ አይደለም፤ ብዙ ሰዎች ለእንጀራ ብለው ሕይወታቸውን ወደአጥርነት ለውጠው ሕይወቱን የሚጠብቁለት ሰው ጦር ቢወረወር አይደርስብኝም ብሎ ሌሎችን ለሞት ቢዳርግ አይደንቅም ይሆናል፤ አጥሩን ጥሶ ወደሱ የሚገሰግስ ሞት ሲያይ ቢፈረጥጥም አያስደንቅም፤ ሆኖም የሞት መንገድ ከጎን ብቻ ሳይሆን ከላይም ሊሆን እንደሚችል አለማወቁ ቀላል አለማወቅ አይባልም፡፡Mesfin Woldemariam
ባህላችን ገዳይን የምናከብር፣ ለገዳይ የምንዘፍን ሕዝብ ቢያደርገንም፣ በድንቁርና ዘመን የነበረውን ይዘን ዛሬ ትንፋሽ የማትችለዋ ቢምቢ ሰውን መግደል እንደምትችል እያወቅን ለገዳይ ብንዘፍን ለሰውነታችን ውርደት ይሆናል፤ ይህንን ብለን ጉዳዩን እንዳንዘጋው በመግደል ልቡ የደነደነ፣ በድን ያልሆነለትን ሁሉ መግደል ልማዱ የሆነ፣ ከመግደል በቀር እምነቱን የሚገልጽበት መንገድ የሌለው፣ ከመግደል ሌላ እንጀራ የሚበላበት ሙያ የሌለው … እንዲህ ያሉ ሰዎች ሁሉ ተሰባስበው መገዳደልን የኑሮአቸው ዓላማና ዘዴ ሲያደርጉ በዝምታ መቀበል፣ ማለት አባቱ ሲገደል ልጁ ዝም ሲል፣ ባልዋ ሲገደል ሚስት ዝም ስትል፣ … ማንም ሰው አለፍርድ ሲጠቃ እያዩ ዝም ማለት ገዳዮችን ያራባል እንጂ ግድያን አያቆምም፤ እንዲህ ያለው በመንፈስ የሞቱ የበድኖች ዓለም ነው፤ በአውሬዎች ዓለም ጉልበት ያለው ደካማውን እየበላ ይኖራል፤ የተፈጥሮ ሕግ ነው፤ የሰው ልጅ በዚህ በአውሬዎች የተፈጥሮ ሕግ አይመራም፡፡
የሰው ልጅ በተፈጥሮ ሕግ የማይመራበት ምክንያት ምንድን ነው? አውሬዎች አያስቡም፤ የሰው ልጅ ግን ያስባል፤ የሰው ልጅ አእምሮ አለው፤ አእምሮ ስላለው ያስባል፤ ያስባል ማለት ከተግባር በፊት ትክክለኛውንና ስሕተት ያለበትን ለይቶ ያውቃል፤ ይህ የተፈጥሮ ሕግ አይደለም፤ የሰው ልጅ ሕግ ነው፤ ያሰበውንም ይናገራል፤ የሚወደውንና የሚጠላውን ስሜቱን ለይቶ ይናገራል፤ የሰው ልጅ ኅሊናም አለው፤ ‹‹ሌሎች ለአንተ እንዲያደርጉልህ የምትፈልገውን አንተም ለሌሎች አድርግ!›› ይላል፤ ይህ የተፈጥሮ ሕግ አይደለም፤ የሰው ሕግ ነው፤ ስለዚህም መግደል፣ በተለይም የመግደል ሱስ፣ የአራዊት እንጂ የሰው ልጅ የችግር መፍቻ ዘዴ አይደለም፤ አራዊት የሚገድሉት ሊበሉ ነው፤ ሰውም ወደአራዊትነት ሲለወጥ የሚገድለው ሊበላ ነው፤ እዚህ ላይ ሰውና አራዊት ይመሳሰላሉ፡፡
በመሠረቱ የመግደል ዓላማ ዝም ለማሰኘት ነው፤ ድንቁርና ነው እንጂ ካፍ ከወጣ አፋፍ ነውና የሚጠሉት ሀሳብ በሌላ ሰው አንደበት ይደገማል፤ መግደል የመጨረሻውን ዝምታ የሚያስከትል ቢሆን ክርስትናም እስልምናም 2007 ዓ.ም. አይደርሱም ነበር፤ ገዳዮች ሰዎችን ሁሉ ጨርሰው ብቻቸውን በመቅረት የሚያገኙት ጥቅም እንደሌለ ስለሚያውቁ የመግደል አማራጮች በሆኑ ሌሎች ዘዴዎች ይጠቀማሉ፤ አንዱ ማሰቃየት ነው፤ ሌላው ማሰር ነው፡፡
ሰዎችን በሀሳብና በእምነት ገባር ለማድረግ ጉልበተኞች የሚጠቀሙባቸው ዘዴዎች መግደል፣ መግደል አላዋጣ ሲል ማሰቃየት፣ ማሰቃየት አላዋጣ ሲል ማሰር፣ ማሰር አላዋጣ ሲል አስሮ ማሰቃየት ነው፡፡
አውሬነትን የተላበሱ ሰዎች የማይገባቸው አንድ ነገር አለ፤ የሚጠሉትና ሰዎችን እስከመግደል፣ እስከማሰርና ማሰቃየት የሚያደርሳቸው ነገር በውስጣቸው ተቀብሮ አለ፤ ነፍሳቸው ከዚያ ነገር ጋር ተቆራኝታለች፤ በመጨረሻም የሚሸነፉት በዚያው ነፍሳቸው ውስጥ በተቀበረው ነገር ነው፤ በውስጣቸው የተቀበረው ነገር አስገድሎ አስገድሎ በመጨረሻ ይገድላቸዋል፤ ጥላቻም አስገድሎ አስገድሎ ይገድላል! በጥላቻና በመጋደል ሰላም አይገኝም፤ ‹‹ለክፉዎች ሰላም የላቸውም ይላል እግዚአብሔር!›› (ኢሳይያስ 48/22)
መንገዱን ጨርቅ ያድርግልን! ለሰላም!
መንገዱን ጨርቅ ያድርግልን! ንስሐ ለመግባት!
መንገዱን ጨርቅ ያድርግልን! ይቅር ለእግዚአብሔር ለመባባል!
የዛሬ ዕብሪተኞች የሙሶሊኒን (ተዘቅዝቆ የተሰቀለውን)ና የጋዳፊን ቦይ ውስጥ ተወትፎ የተገኘውን አስበው ልባቸውን ለምሕረትና ለእርቅ እንዲከፍቱና ለልጆቻቸው የፍቅርና የመተማመን ዘመን እንዲያውጁ እግዚአብሔር መንፈሳዊ ወኔ ይስጣቸው፡፡

በጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው የሽብር ክስ ዝርዝር

Ethiopia Human Rights Project
የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10/2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው ክስ የጸረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡Getachew Shiferaw
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡
በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣተቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26/2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡