Friday 17 January 2014

አቡጊዳ – ሰማያዊ ፓርቲ በጎንደር ከተማ በድንበሩ ጉዳይ ሰልፍ ሊጠራ ነው

በኢትዮጵያ ዉስጥ በምርጫ ቢርድ ተመዝግቦ እየተንቀሳቀስ ያለው የሰማያዊ ፓርቲ ፣ በጎንደር ከተማ ሕዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ለመጥራት እየተዘጋጀ እንደሆነ ፓርቲዉ በፌስ ቡኩ ገጽ ባወጣው መግለጫ ገለጸ።

«ሕወሓት ኢህአዴግ በህገ ወጥ መንገድ ሉዓላዊ መሬታችንን ለሱዳን መንግስት አሳልፎ አሳልፎ ለመስጠት እያደረገ ያለውን ህገወጥና ሀገር ቆርሶ የመስጠት ወንጀል በመቃወም ሰማያዊ ፓርቲ እሁድ ጥር 25 2006 ዓ.ም በጎንደር ከተማ ታላቅ ህዝባዊ ሰልፍ ማዘጋጀቱን የፓርቲው ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ብርሀኑ ተክለ ያሬድ ገለፁ፡፡የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው አያይዘው እንደገለፁት ቅዳሜ ጥር 17 2006 ዓ.ም በፓርቲው ፅህፈት ቤት የፓናል ውይይት እንደሚደረግና በነዚህ ፐሮግራሞች ላይም የፖለቲካ ፓርቲዎች የሲቪክ ተቋማትና ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንዲሳተፍ ጥሪ አስተላልፈዋል»
ሲል በሰልፉ ሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶ፣ የሲቪክ ማህበራት እንዲተባበሩ ጥሪ አቅርቧል። የሰማያዊ ፓርቲ ምን ያህል በጎንደር ሰልፍ ዙሪያ፣ ከሌልቾ ተቃዋሚዎች ጋር ምክክር እንዳደረገ እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም። በሰኔ 2005 ዓ.ም ወቅት ሰማያዊ፣ በሕዝብ ዘንድ የበለጠ እንዲታወቅበት ያደረገውን የአዲስ አበባን ሰልፍ፣ መኢአድ እንዲጉሁም የአንድነት ፓርቲ ድጋፉቸዉን ሰጥተዉ እንደነበረ ይታወቃል።
ከዚያም በኋላ ከሰኔ 2005 ዓ.ም እስከ መስከረም 2006 ዓ.ም ፣ የአንድነት ፓርቲ በተለያዩ የአገሪቷ ግዛቶች የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት በሚል እንቅስቃሴ ሥር በጠራቸው ሰላማዊ ሰልፎች፣ የሰማያዊ ፓርቲ ለርሱ ድጋፍ እንደተደረገለት፣ የአጸፋዉን ድጋፍ አለመስጠቱ የሚረሳ አይደለም። በተለይም በመስከረም በአዲስ አበባ የተደረገዉን እና አንድነት ፓርቲ የጠራዉን ሰላማዊ ሰልፍ ፣ ሰላሳ ሶስቱ በሚባለዉ ስብስብ ዉስጥ ያሉ ድርጅቶች ሲቀላቀሉት፣ ሰማያዊ ፓርቲ ግን ፣ ከሌሎች ጋር አብሮ ከመስራት፣ በተናጥል የራሱን ሰልፍ በመጥራቱ ብዙዎችን አላስደሰተም።
የአንድነት ፓርቲ ለአማራዉ ክልል አስተዳዳሪና ለአቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ በድበቅ፣ በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያ እየተሰራ ያለዉን ጉዳይ በተመለከተ፣ በአስቸኳይሁሉም ነገር ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን መጠየቃቸው፣ በዚህም ዙሪያ ፓርቲዉ በአዲስ አበባ ሕዝቡን ለማወያየት ዝግጅት እያደረገ እንደሆነም በቅርቡ ተዘግቧል።
በጎንደር ከተማ አንድነት ከአራት ወራት በፊት ባደረገዉ ሰላማዊ ሰልፍ ከ40 ሺሆች በላይ የሚሆን ሕዝብ መገኘቱ ይታወሳል።
የሰማያዊ ፓርቲ ከብቻ ጉዞ ተቆጥቦ፣ ይህ የኢትዮ-ሱዳን ቦርደር ፣ ሁሉንም ኢትዮጵያዉያን የሚመለከት አንገብጋቢ የአገር ጉዳይ መሆኑ ተረድቶ፣ በአስቸኳይ ፣ ከአንድነት፣ መኢአድና ከመሳሰሉ ፓርቲ አመራሮች ጋር በመነጋገር፣ ጥር 25 2006 ዓ.ም የሚደረገዉን ሰልፍ በጋራ ማቀናበር እንዳለበት የሚናገሩ አንድ የፖለቲካ ተንታኝ፣ «የድርጅት መሪዎች ከድርጅታዉ ጥቅምና ዝና ይልቅ ለአገር ማሰብ እንዳለባቸው ማወቅ አለባቸዉ። ከሰማያዊ ፓርቲ በፊት ኢትዮጵያ ትቀድማለች።ከአንድነት ፓርቲ በፊት ኢትዮጱያ ትቀድማለች። ከመኢአድ በፊት ኢትዮጵያ ትቀድማለች። ከአረና በፊት ኢትዮጵያ ትቀድማለች» ሲሉ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዉያን ሁሉ በዘር፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ ፓርቲ ልዩነት ፣ ሳይከፋፈሉ ለኢትዮጵያ እንዲቆሙ ጠይቀዋል።

No comments:

Post a Comment