Monday 10 March 2014

የአባ መላ ነገር… “እዛም ሄደሽ በላሽ፣ እዚ’ም መጥተሽ በላሽ…” (በደረጀ ሃብተወልድ)

እዛም ሄደሽ በላሽ፣ እዚ’ም መጥተሽ በላሽ፣
ላ’መልሽ ነው እንጂ፣ ሆድሽን አልሞላሽ።”
አባ መላ የሚባለው ሰውዬ ከወራት በፊት፦ አለቆቹን እየተሳደበ ከኢህአዴግ ካምፕ ወደ ተቃዋሚው ጎራ ተቀላቀለ። በተቃውሞው ካምፕ የጥቂት ወራት ቆይታው “ስለ ኢህአዴግ የማወጣው ብዙ ምስጢር አለ” በሚል የማጓጊያ እጅ መንሻ የሆነ ነገር ለማግኘት ፈለገ። ሆኖም ከስድብና ከተረብ ውጪ ምንም የማናውቀውን አዲስ ነገር ሳይነግረን እነሆ በጥቂት ወራት ልዩነት እንዳመጣጡ ዲያስፖራውንና ተቃዋሚዎችን እየተሳደበና እንደ ልማዱ “ስለ ዲያስፖራው የማውጣው ብዙ ምስጢር አለ” የሚል የማጓጊያ እጅ መንሻ እያቀረበ ወደ ቀድውሞ ቤቱ መመለሱን አውጇል።
ከዕድሜው አኳያ የነ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን እኩያ እንደሆነ ሲናገር የሰማነውን ሰውዬ ይህን ያህል አክሮባት እንዲሠራ ምክንያት የሆነውም፤ ረዳት አብራሪ ሀይለመድህን አበራ አውሮፕላን መጥለፉን ተከትሎ በአንዳንድ የዲያስፖራ አክቲቪስቶች በኩል ድጋፍ መታዬቱ ነው ይለናል።
በዚህ ጉዳይ ላይ በሀሳብ መለያዬት ጠቅላላ አቋምን ለመቀየር ምክንያት ሲሆን እስኪ አስቡት። ይህ የሚያሳዬን ሰውዬው የውስጥ እምነት ወይም አቋም የሚባል ነገር የሌለው ሰው መሆኑን ነው።
አዎ! “አመለካከት” ወይም “አቋም” የሚባለው ነገር፤ እንዲህ በምኑም፣በምኑም ሸብ ሲያደርጉት ከግራ ወደ ቀኝ የሚገለባበጥ የአህያ ጭነት አይደለም!
ነገሩ ወዲህ ነው። አባ መላ ኢህአዴጎችን እየሰደበ ወደ ተቃዋሚው ጎራ ሲቀላቀል “አገኛለሁ” ብሎ ያሰላው ጥቅም ነበር። ሆኖም ሀሳብን በነፃነት ለመግለጽ ከሚያስችል ነፃ መድረክ ውጪ ሌላ ነገር ሊያገኝ አልቻለም። ባገኘው ነፃ መድረክም ማንም ሳይቆነጥጠው ከትንሽ እስከ ትልቅ የቀድሞ አለቆቹን እስከ ዶቃ ማሰሪያቸው ነግሯቸዋል። እኛንም አስቆናል። ስንስቅለት ጨምሮ ጨማምሮ አቅምሷቸዋል። እኛም፦“የአገሩን ሰርዶ ባ’ገሩ በሬ” እያልን ተዝናንተናል።
ከዚያ ባለፈ ግን ለቁም ነገር ያሰበው ሰው ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ።
እናም ሁሉንም ሲያየው የጥቅም በሮች ሁሉ ጨርሰው ተቀርቅረዋል።የመጣበት ቦታ እንዳሰበው ጥቅም የሚግበሰበስበት አለመሆኑን አስተዋለ። የተመኛቸውን ቦታዎችም ሊያገኛቸው አልቻለም። ወደ ዲያስፖራው ለመቀላቀል ውሳኔ ሲያሳልፍ ያሰላው የጥቅም ስሌት ሳይሠራ ቀረ፤ እናም “ …የቀድሞ ቤቴ ይሻለኛል” አለ። የኢህአዴግን የንስሀ ቄደርም በመምሬ “ቤን” ተረጨ።“ውጪ አገር ቢከዱ ማክዶናልድ ምግብ አቅራቢነት ከመቀጠር ውጪ ምን ሙያ አላቸው?” ብሎ የተረባቸውን የኢህአዴግ አለቆቹንም ፦”…ባለፉት ጥቂት ወራት በያዝኩት አቋም ያስቀየምኳችሁ የቀድሞ ወዳጆቼ ይቅር በሉኝ” ብሎ በኑ ተማፀነ።
“የዓባይ ግድብ በህወሀቶች ሚሊየን ዶላር እየተዘረፈበት ያለ ፕሮጀክት እንደሆነ መረጃዎች አሉኝ” እያለ ከጥቂት ወራት በፊት ሲያወራ የሰማነው ሰውዬ፤ ዓባይን እቦታው ድረስ ሄዶ ድንጋይ እያጋዘ መገደብ እንደሚፈልግ ተናገረ።
እንዲህም አለ።
ነፍስ ይማር!

No comments:

Post a Comment