Saturday 5 April 2014

ህወሓት በአፅቢ (እንዳስላሴ) ረብሻ ለመቀስቀስ እየሞከረ ነው፤ ነገ እሁድ አረና ለጠራው የተቃውሞ ሰልፍ ቅስቀሳውን ቀጥሏል

አብርሃ ደስታ ከመቀሌ
የዓረና አባላት ለነገ እሁድ መጋቢት 28 በአፅቢ (እንዳስላሴ) ከተማ ለሚደረግ ህዝባዊ ስብሰባ ቅስቀሳ እያደረጉ ይገኛሉ። በዓድዋ ቅስቀሳ ስናደርግ “እንዳትነኳቸው፣ በሰላም ይቀስቅሱ!” ብሎ መመርያ የሰጠ በመቐለ ከተማ የሚገኝ የህወሓት ከፍተኛ አመራር ዛሬ በአፅቢ ከተማ በምናደርገው ቅስቀሳ ረብሻ እንዲነሳ መመርያ መስጠቱ ከአንድ ሰዓት በፊት ሰማሁ። አላመንኩም ነበረ። ለማረጋገጥ ወደ አፅቢ ደወልኩ።
የዓረና አባላት ቅስቀሳ ሲያደርጉ ገብረማርያም የተባለ የወረዳው የሚልሻ አዛዥ ወጣቶችን አሰባስቦ የሚታደለውን ወረቀት መቅደድና መሳደብ መጀመራቸው ተነገረኝ። በራሪ ወረቀቱ መቅደድና መሳደብ የጀመረው የወረዳው ዋና አስተዳድሪ ሲሆን እሱን ተከትለው የሚረብሹ የተደረጁ ወጣቶችም ነበሩ። አሁን ህዝቡ ጣልቃ ገብቶ የሚረብሹ ወጣቶችን አስፈራርቷል። ዋና አስተዳዳሪውን በህዝብ ተሰድቧል። አሁን ሁኔታው ተረጋግተዋል። አቅጣጫው ግን በተደራጀ መልኩ የሚከናወን የዓዲግራትን ዓይነት ይመስላል። በአፅቢ ወንበርታ በጣም ብዙ የዓረና አባላትና ደጋፊዎች አሉ። ከወራት በፊት ህወሓትን ተቃውመው ዓመፅ አስነስተው እንደነበር ይታወሳል። አሁን ወደ አፅቢ እየሄድኩ ነው።
የተጋላቢጦሽ! ተቃዋሚ ፓርቲ ሰላምና ፀጥታ እንዲከበር ጥረት ሲያደርግ ገዥው ፓርቲ (መንግስት) ደግሞ ረብሻ ለመቀስቀስ ጥረት ያደርጋል፤ ስልጣኑ ተጠቅሞ የህዝብን ሰላም የሚበጠብጡ ወጣቶች በክፍያ ያደራጃል፣ ሰለማዊ ሰው እንዲደበድቡ ያበረታታል። ዓመፅ መቀስቀስ ለምዷቸው ይሆን?! ዓረና ግን ሰለማዊ ፓርቲ ነው። ለህዝብ ነፃነት ስንል እንደበደባለን፤ ለሰላም ስንል መስዋእት እንሆናለን። ምክንያቱም የሰላም መንገድ ሰለማዊ መሆን መሆኑ እንረዳለን። ትግሉ ስንጀምር ብዙ መስዋእትነት እንደሚያስከፍለን እናውቃለን። የአፅቢ ህዝብ እንደሚተባበረንም እርግጠኞች ነን።

No comments:

Post a Comment