Tuesday 12 August 2014

የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው፣ የመኢአድ እና የአንድነት ዉህደት እንደማይፈልጉ በመገልጽ የዉህደት አመቻች ኮሚቴን እንዳፈረሱ መረጃዎች ይጠቁማሉ። – አልዩ ተበጀ

አብዛኞቻችን የአንድነት እና መኢአድ ዉህደት ተጠናቆ፣ በአዲስ መንፈስ የሚሊዮኖች ድምጽ ንቅናቄን እንቀጥላለን የሚል ተስፋና ጉጉት ነበረን። የኢትዮጵያዉያንን መተባበር የማይፈልገው ሕወሃት/ኢሕአዴግ፣ በሚቆጣጠረው ምርጫ ቦርድ አማካኝነት፣ ዉህደቱን ለማጉዋተት እንደተለመደው መስራት ጀመረ። «መኢአድ ያላሙዋላቸው ወረቀቶች አሉ» በማለት ዉህድቱን ማድረግ እንደማይችል አሳወቀ። (የተለመደው የማሰናከል እጁት ተግባር) መኢአድ ሕዝብ ያውቀው ዘንድ፣ ያለውን ሁኔታ ለማሳወቅ መግለጫ አወጣ። በጉዳዩ ላይም ከምርጫ ቦርድ ጋር ስብሰባዎች በማድረግ ከመፍታት ጀምሮ ሌሎች አማራጮችን እየፈለገ ዉህደቱን ለማሳካት በስፋት መንቀሳቀስ ጀመረ።
ከመኢአድ ጋር ዉህደት ለማድረግ ከ2 ፣ 3 አመታት በላይ ንግግሮች ሲደረጉ ነበር። አገዛዙ የደነቀረዉን ትንሽ እንቅፋት ለማስወገድ አንድ ወይንም ሁለት ሳምንት መጠበቁ ችግር የሚኖረው አይመስለኝም። ነገር ግን እንደ አንድነት ደጋፊ እጅግ በጣማ ያሳዛነኝ እና ልቤን ያደማው ክስተት ተፈጸመ።
የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው፣ ለብዙ አመት የተደከመበትን፣ የዉህዱ ሰብሳቢ ሊቀመንበር የነበሩት አቶ ሃብታሙ አያሌው የታሰሩበትን ፣ በአገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን በጉጉትና በተስፋ የምንጠብቀዉን፣ ምርጫ ቦርድ ካስቀመጣት ትንሽ መሰናክል ዉጭ፣ ሁሉም ነገር ያለቀለትን፣ የመኢአድ እና የአንድነት ዉህደት እንደማይፈልጉ በመገልጽ የዉህደት አመቻች ኮሚቴን እንዳፈረሱ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
በሚኔሶታ ቤተክርስቲያን ስሄድ ፣ የአንድነት ድጋፍ ድርጅት አስተባባሪ መሆኔን የሚያዉቁ ሲያገኙኝ ፣ አንድነት ከመኢአድ ጋር የሚያደርገውን እንቅስቅሴ እንደተደሰቱ ነበር በስፋት የሚነግሩኝ። ህዝቡ፣ ደጋፊው ስሜቱ በጣም ተጋግሎ ነበር። በአሁኑ ጊዜ የሕዝቡ መከራ በበዛበት፣ አንድነት ፓርቲ ሌሎችን እያሰባሰበ፣ የተጀመረዉን የሚሊዮኖች ንቅናቄ ይቀጥላል ብለን ስንጠብቅ፣ ያለ ምንም በቂ ምክንያት ሕወሃት/ወያኔ ትንሽ መሰናክል ስላስቀመጠ ብቻ ፣ በየክልሉ ያሉ አባላትና ደጋፊዎች እየፈለጉት፣ ዉህደቱ እንዲቆም ማድረግ በጣም፣ እጅግ በጣም ትልቅ በደል ነው።
በአንድነት እና በመኢአድ መካከል፣ ዉህደት እንዲደረግ ቁልፍ ሚና ከተጫወቱት ወገኖች መካከል አንዱ፣ በሕወሃት/ኢሕአዴግ እጅ ስር ታስሮ የሚገኘው ሃብታሙ አያሌው ነው። ሃብታሙ አያሌ ከኢንጂነር ግዛቸው ጋር ብዙ ይከራከር የነበረና ኢንጂነሩም ለሚሰራው ስራ መሰናክል ሆነውበትም እንደነበረ ይታወቃል። ከአምስት አመታት በፊት፣ ኢንጂነር ግዛቸው ከትናትናው “ዝም አንልም” የዛሬው በአብዛኛው የሰማያዊ አመራሮች አባል ከሆኑት ጋር ተመሳሳይ ችግር እንደነበረባቸው የሚታወቅ ነው:: እነዚህን በርካታ ወጣት የቀድሞ የአንድነት አመራሮችን፣ እንዲሁም እንደ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም ያሉትን ማባረራቸው ይታወቃል። ያኔ ፓርቲው ተከፋፍሎ በትግሉና በታጋዮች ሞራል ዘንድ ምን ያህል ከፍተኛ አሉታዊ ተጽእኖና ጉዳት እንዳመጣም የሚታወቅ ነው።
ኢንጂነር ግዛቸው የመኢአድ እና የአንድነት ዉህደት እንዲኖር ፍላጎት ብዙ እንዳልነበራቸው የሚናገሩ አሁንም ጥቂቶች አልነበሩም። (ዉህደቱ ከተሳካ ሊቀመንበር የመሆን እድላቸው በጣም የመነመነ በመሆኑ) የምርጫ ቦርድንም ተንኮል ሳያጡት ቀርተው አደለም፣ ምርጫ ቦርድ ለአገዛዙ እንደሚሰራ እያወቁ፣ ምርጫ ቦርድ የሚያቀርባቸውን እንቅፋቶች እንደ ሰበበ በመቁጠር የዉህደት አመቻች ኮሚቴዉን ማፍረሳቸው፣ እንደ አንድ የአንድነት ደጋፊ ልረዳው የማልችለው ጉዳይ ነው። በሚሊዮኖች ዘመቻ የተነሳሳዉን፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ኢትዮጵያዊ ወኔ ለማኮላሸት፣ ከትግሉና ከአገር ጥቅም ይልቅ የራሳቸውን ስልጣን ብቻ በመፈለግ ለሕዝብ ጥያቄ ንቀታቸውን በመግለጽ ትልቅ ጥፋት እያደረጉ ናቸው።
ሕዝቡ አብሮ መስራትን ይፈልጋል። የመኢአድ እና አንድነት ዉህደትን ይፈልጋል። የማይፈልጉት አምባገነኖች ብቻ ናቸው። ኢንጂነር ግዛቸውና ለርሳቸው ድምጽ የሰጡ የአንድነት የምክር ቤት አባላት፣ «ሕወሃት/ሕአዴግን የሚያስደስተዉን ነው ወይስ ህዝቡ የሚያስደስተው ማድረግ የምትፈልጉት ?» ለሚለው ጥያቄ በግልጽ ሊመልሱ ይገባል።
በኢንጂነር ግዛቸው የተወሰደው ሕወሃት/ሕአዴግን ብቻ የሚጠቅም እርምጃ በአስቸኩዋይ ተቀልብሶ ፣ አንድነት ከመኢአድ ጋር የጀመረዉን ዉህደት አጠናቆ፣ ሕወሃት/ኢሕአዴግ አፍሮ፣ ትግሉ ወደፊት መዉሰዱ ብቸኛ አማራጭ ነው።
ኢንጂነር ግዛቸው ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ችግር አላቸው። አሁን ደግሞ ከመኢአድ ጋር ከተጣሉ፣ ታዲያ እመራዋለሁ የሚሉት አንድነት ከማን ጋር ነው አብሮ የሚሰራው ? በዘር ከተደራጁ ድርጅቶች ጋር ? ወይስ ተመልሰው ወደ መድረክ በመግባት የ2002ቱን ሩጫ ሊደግሙልን ነው ?
የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች፣ እኛ በሚሊዮኖች የምንቆጠር ነን። ወሳኝ ጊዜ ላይ ነው ያለነው። ጥቂቶች ንቅናቄያችንን ወደሁዋላ ሊጎትቱ አይገባም።በመሆኑም ከመቼዉም ጊዜ በላይ ድምጻችንን ማሰማት አለብን። የአንድነት ፓርቲ የኢንጂነር ግዛቸው ብቻ ሳይሆን የሚሊዮኖች ነው። በደሴ፣ በጎንደር፣ በአርባ ምንጭ፣ በናዝሬት፣ በባህር ዳር፣ በአዳማ ..የምንኖሩ የአንድነት አባላትን የክልል አስተባባሪዎች፣ በዉጭ አገር ያለን ድምጻችንን እናሰማ። በየአካባቢያችን ከመኢአዶች ጋር አብረን በስራ ተዋህደን እየሰራን ነው። አብረን እየታሰርን፣ አብረን እየተደበደብን ነው። አገዛዙ ከሚያደርገው በማይተናነስ ሁኔታ ኢንጂነር ግዛቸውና ከርሳቸው ጋር የቦደኑ ጥቂቶች እንዲከፋፍሉን መፍቀድ የለብንም። አንድነታችንን ለማሳየት የምርጫ ቦርድ ወረቀት አያስፈልገንም። ትግሉን ተያይዘን መቀጠል አለብን። ትግሉ የሚሊዮኖች ንቅናቄ ነው። ትግሉ ወደፊት እንጂ ወደ ሁዋላ አይሄድም ።udJAEUP

No comments:

Post a Comment