Tuesday 2 December 2014

ይድረስ ለጎንደር ሕዝብ

በተለያዩ ዘመናት በአገራችን ወደ ሥልጣን የመጡት ገዥዎች፤ ሕብረተሰባችን ከፋፍሎ ለመግዛት እንዲያመቻቸው የዘር ግንድ እየቆጠሩ አንዱን ከሌላው የተሻለ አስመስሎ በመሳል፤ አንደኛውን በሌላኛው ወግን ላይ በስነልቦና ቂም እያናከሱ፤ የግፍ ግዛት ዘመናቸውን አሳልፈው አሁን ከአለንበር ዘመን ደርሰናል። በአሁኑ ጊዜ በሥልጣን ላይ የተፈናጠጠው መንግሥት ደግሞ ገና ከጅምሩ ወደ ሥልጣን ሲመጣ በረቀቀ ተንኮል የኢትዮጵያን ሕዝብ በዘር ሐረግ ከፋፍሎ ለመግዛት እንዲያመቸው አንቀጽ 39ኝን በሕገመንግሥት አጽድቆ ለረዥም ዘመን በጋራ ሕብረተስባዊ ገመድ ተሳስረው የኖሩትን ኢትዮጵያዊያን በጎሳ በመከፋፈል በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ያሉ ብሔረሰቦች ተፈጥሮአዊ የሆነውን እና ሊከባበሩበት የሚገባውን ማንነታቸውን ጦርና ጋሻ አድርገው እንዲዋጉበት በማድረግ ነው የሥልጣን እድሜውን እያራዘመ ያለው።
(ጎንደር ፋሲል ግምብ - ፎቶ ፋይል)
(ጎንደር ፋሲል ግምብ – ፎቶ ፋይል)

ታዲያ ይህ መንግሥት ለአገራችን ሰላም ያመጣል በሚል ከፋፍሎ ለመግዛት እራሱ በቀመረው የጎሳ ክልል ቀቢጸ ተሥፋ “በብሔሮች” ራሥን በራሥ የማሥተዳደር ሥም፤ አብሮ የኖረውን እያራራቀ፤ ተፈቃቅዶ ይኖር የነበረውን እንደጠላት እያሥተያዬ፤ አካባቢያዊ ሰላምን እያደፈረሰ፤ እርሥ በርሥ እያጋደለ ያለው ትልቁ ችግር በአገራችን ላይ የተደነገገው ህገመንግሥታዊ አደጋ፤ ከሃያ ሦስት ዓመት በኋላ ህግ አውጭውን አካል እና መንግሥታዊ መዋቅሩን በማሥጨነቅ እርስ በራሱ ሲያተራምስ እያየን ነው። በመሆኑም፤ ባለፈው ሚያዝያ ወር ባወጣነው እና በድህረ-ገጽ ለማሳነበብ እንደሞከርነው ሁሉ፤ አሁንም በድጋሚ የምናሥገነዝበው፤ መንግሥታት መጥተው፤ መንግሥታት ሲያልፉ፤ የማያልፈውን የቅማንት እና የአማራ ህብረተሰቦች የጋራ ታሪክ ዘመኑ ባመጣው የጎሳ ፖለቲካ ጉንፋን መሰል አሥተሳሰብ እና ድርጊት የኋላ ታሪካቸውን ማጥቆር እና የወደፊቱንም ማህበራዊ ግንኙነታቸውን ማጨለም አይገባም እንላለን።
ሰለዚህ ይህን አገር አፍራሽ፤ ሰላም አደፍራሽ የሆነውን አንቀጽ 39ኝን እንደ መብት ማስከበሪያ በመጠቀም የቅማንት የማንነት እና ራሥን በራሥ የማሥተዳደር ጥያቄ ያነሱ የቅማንት ተወላጅ ወገኖቻችን ያልተገነዝቡት ነገር፤ ተዋልዶና ተጋብቶ፤ አንድ ሐይማኖት አምልኮ ለረዥም ዘመን ከኖረው ወገናቸው ጋር አብሮ የማያኗኑር መሆኑ ነው። ቅማንት እና አማራ ጊዜ እና ቦታ አንድ ላይ ያሥቀመጣቸው ብቻ ሳይሆኑ፤ እጅግ ብዙ የጋራ ችግር እና ደሥታን ጽዋ አብረው የተጎነጩ፤ ረዥም የታርክን ጎዳና አብረው የተጓዙ፤ እምነትና ቋንቋ ባንድ ገመድ ያስተሳሰራቸው ሕዝቦች መሆናቸውን ነው። ይህ ሲባል ግን፤ መለሥተኛ ችግሮች ተከስተው አያውቁም ማለት አይደለም። በሁለቱ ህብረተሰቦች መሃከል የነበረው ችግር ግን፤ በሁለት ወንድማሞች መካከል ከሚከሰት ችግር የተለዬ አልነበረም። ስለሆነም ነው በየጊዜው የሚፈጠሩ መለሥተኛ ችግሮቻቸውን በጋር እየፈቱ እና መቻቻልን መሰረት አድርገው የአንድነታቸውን ታሪክ ጠብቀው ከዚህ የደረሱት። ወደፊት ማደግና መቀጠልም ያለበት በዚሁ መንገድ ነው። ይህ ደግሞ በማንኛውም የህብረተሰብ ክፍል ያለ እና የሚኖር ነው።
ይህን ሥንል ግን፤ የቅማንት ብሔረሰብ ወገኖቻችን ይህን ጥያቄ ያለ ብሶት አነሱት በማለት በጭፍን ለመኮነን አይደለም። ሆኖም፤ በኛ እይታ፤ አሁንም በድጋሚ ማሥገንዘብ የምንፈልገውው፤ ችግሩ የመልካም አሥተዳደር በደል እንጂ፤ ለቅማንቱ ችግር ምንጭ አማራው አይደለም። ለአማራውም ችግር ምንጭ፤ ቅማንቱ አይደለም። ይህ የአሥተዳደር በደል ቅማንቱ ራሱን ሥለከለለ ይፈታል ብሎ ማሰብ፤ እጅግ ሥህተት ነው። በመላ አገሪቱ የተንሰራፋው የአሥተዳደር በደል፤ በመላ አገሪቱ ሳይፈታ፤ ለአንድ ጎሳ ብቻ ነጻ እና ዲሞክራሲያዊ መብት እንደ መና ከሰማይ ሊወርድ አይችልም። እሁን እዬተሄደበት ባለው መንገድ ሊመጣ የሚችል ለውጥ ቢኖር፤ በአካባቢው ባልተወለዱ ባልሥልጣኖች ከመበዝበዝ ይልቅ፤ ከራሳችን በተወለዱ መሪዎች መበዝበዝን ነው። ምክንያቱም በዬትኛውም የአገራችን የጎሳ ክልልን እንደ ነጻነት ቆጥረው በተግባር ለማዋል የሞከሩት አካባቢዎች ያተረፉት ሃቅ ይህ ሲሆን አይተናል እና።
ስለሆነም፤ በሰሜን አሜሪካ የምንኖር ጉዳዩ ያገባናል የምንል የቅማንት ብሔረሰብ ተወላጆች፤ በአገር ቤት የተወሰኑ የቅማንት ተወላጆች፤ ያነሱት የማንነት እና የራሥን በራሥ ማሥተዳደር ጥያቄ አለመመለሥ ምክንያት በተወሰኑ ግለሰቦች መካከል እርሥ በርሥ መተነኳኮስ መጀመሩን ሰምተን እጅግ በጣም አዝነናል፤ ቀጣዩም አሳስቦናል። የዚህን ጥያቄ አደገኛነት ባለፈውም ጠቁመናል፤ እሥከ የት ሊዘልቅ እንደሚችልም አመላክተናል። አሁንም በድጋሚ ያለፈውንም ሆነ የወደፊቱን የጋራ ባህላችን እና የጋራ አካባቢያዊ የኑሮ ዘይቤ አበላሽቶ እና መጥፎ አሻራ ጥሎ የሚያልፍ መሆኑ መገንዘብ ያስፈልጋል።
አሥተሳሰቡ እና ድርጊቱ፤ ሁሉንም የሕብረተሰብ አባሎች የማይወክል እንደሆነ ብናውቅም፤ የሁኔታው መከሰት ግን፤ በራሱ አሥደንጋጭ እና አሳዛኝ፤ እንዲሁም አሳፋሪም ጭምር ነው። ይህ የወያኔ/ኢህአዴግ መንግሥት ባመጣው የጎሳ ወጥመድ ውስጥ የገቡ ወገኖች የሚያራምዱት አስተሳሰብ አስከፊ ውጤት ሊሆን የሚችለው፤ መንግሥታት መጥተው፤ መንግሥታት ሲያልፉ፤ የማያልፈውን የሁለቱ ህብረተሰቦች የኋላ ታሪካቸውን ማጥቆር እና የወደፊቱንም ማህበራዊ ግንኙነታቸውን ማበላሸት ብቻ ነው።
እንዲህ አይነቱ ለማንም ወገን የማይጠቅም ልብ የሚኢያሻክር ድርጊት በአስቸኳይ መቆም አለበት። ይህን በማለታችን እንደ ድፍረት ሊያሥቆጥርብን አይገባም። እኛም ለተወለድበት አካባቢ፤ ለተፈጠርነበት ህብረተሰብ የሚበጀውን የቅርብ እና የሩቅ ራዕይ የማመላከት ግዴታ አለብን እና። ይሁንና፤ በሁለቱ ሕዝቦች ውሥጥ የሚገኙ ሽማግሌዎች፤ አዋቂዎች፤ እና ምሁራን ሁኔታውን አግባብ ባለው እና በሰከን መንገድ ይፈቱታል ብለን እናምናለን። ከሁሉም በላይ የአካባቢውን ሰላም እና መረጋጋት ታሳቢ አድርገው በሁለቱ ህብረተሰቦች መሃከል ሰላማዊ ንግግር ተጀምሯል የሚል ሰምተናል። ይህ ጅምር ከወዲሁ የሚበረታታ ሲሆን፤ የጋራ ወገኖቻችንን የቆዬ ፍቅር የሚያረጋግጥ ክሥተትም ጭምር በመሆኑ፤ ጠንክሮ እንዲቀጥል በአክብሮት እናሳሥባለን። እኛም የአብሮነት ሂደቱ እና በአካባቢው ሰላማዊ ኑሮ እንዲቀጥል የምንችለውን ሁሉ ለመተባበር ዝግጁ ነን።
በተጨማሪም፤ ማንኛውም ግለሰብ፤ ቡድን፤ ድርጅትም ሆነ የመንግሥት አካል በሥሜት ተገፋፍቶ እና ባለማወቅ ወይም ሁኔታውን ለተለዬ የግል አላማ አሥቦ የሚንቀሳቀስ ቢኖር፤ “አንተ ሰላም እንድትውል ጎረቤትህ ሰላም ይሁን” እንዲሉ፤ የሚፈጠረው የሰላም መደፈረስ ሁሉንም የሚጎዳ በመሁኑ ከመጥፎ ተግባር እንዲቆጠብ ለማሳሰብ እንወዳለን። ህዝቡም፤ የላይ የታች ሳይባባል በአንድ ሆኖ ለጥፋት የሚንቀሳቀሱትን ትክክል አደላችሁም ማለት የሚገባ መሆኑን ጊዜው እያመላከተ ነው። አገር በሰነፎች እንደማይገነባ ሁሉ፤ ሰላምም በነገረኞች አይረጋም እና።
በዚህ አጋጣሚ ሁለቱም ህዝቦች መገንዘብ ያለባቸው አጠቃላይ ሁኔታውን እና የሰሞኑንም ቤተሰባዊ አለመግባባት የፈጠረው የመንግሥት ፖሊሲ እና አሰራር መሁንን ነው። “ውኃው ሂያጅ ደንጊያው ቀሪ” እንደ ሚባለው ሕዝብ ይኖራል መንግሥት ግን ያልፋልና። የሚያልፍ መንግሥት ዘላለማዊ የሚኖር የታሪክ ጠባሳ ጥሎ እንዳያልፍ መጠንቀቅ አስፈላጊ ነው። እያንዣበበ ያለው ችግር ከፍ ሲል የኢትዮጵያ ዝቅ ሲል ደግሞ የጎንዳር ሕዝብ ችግር ነውና አብረን ተባብረን ወደ ሰላም እና የዘር ክልል ያልበከለው ሁለንተናዊ የአንድነት ወንድማማቻዊ ጎዳና እንምራው።
በመጨረሻም፤ “እርቅ፤ ደም ያደርቅ” እንዲሉ፤ የተጣላውን እያሥታረቀ ለዘመናት ራሱን ጠብቆ የኖረ ህዝብ፤ ዛሬም የገጠሙትን ችግሮች በለመደው ባህላዊ የሽምግልና ጥበብ እየፈታ ወደፊት እንዲቀጥል ጥርጥር የለንም። ለሁሉም ወግኖቻችን እና ሕዝባችን፤ ሰላሙን እና ደህንነቱን የምንመኘው ከልብ ከሚመነጭ ፍቅር እና አክብሮት ጋራ ነው።
ጉዳዩ ይመለከተናል ከምንል የቅማንት ብሔረሰብ ተወላጆች፤ ሰሜን አሜሪካ።

No comments:

Post a Comment