Saturday 23 January 2016

እነ ጌታቸው ሺፈራው ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ተሰጠባቸው

ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ ተደርገናል›› ተጠርጣሪዎች
*‹‹6 ቀን ደንበኛየን ለማግኘት ተመላልሼ ተከልክያለሁ›› የጋዜጠኛ ጌታቸው ጠበቃ አምሃ መኮንን
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
12552925_828856087240051_5210060765143821641_nበሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከታህሳስ 15/2008 ዓ.ም ጀምሮ በማዕካለዊ ወንጀል ምርመራ በእስር ላይ የሚገኙት እነ ጌታቸው ሺፈራው ፍርድ ቤት ቀርበው ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
በእነ ዳንኤል ተስፋየ ስም በተከፈተው የምርመራ መዝገብ ስር የተካተቱት ሦስት ተጠርጣሪዎች አቶ ዳንኤል ተስፋየ፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል እና ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ሲሆኑ፣ ተጠርጣሪዎች ዛሬ ጥር 14/2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ቀርበው ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ጠይቆ የ27 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋ፡፡
ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ የጠየቀበትን ምክንያት ለፍርድ ቤት ያስረዳ ሲሆን ‹‹የቴክኒክ ማስረጃዎችን ከብሄራዊ ደህንነትና መረጃ ኤጀንሲ ጠይቀን ማስመጣትና ተጨማሪ ግብረ አበሮችን መያዝ ይቀረናል›› ብሏል፡፡
ተጠርጣሪዎች ከተያዙበት ቀን ጀምሮ በማንም እንዳይጎበኙ መከልከላቸውን በማስረዳት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ‹‹ከተያዝኩ ጀምሮ ቤተሰቦቼን አይቼ አላውቅም፡፡ እስር ላይ ሆኜ በቀን ለ10 ወይም 15 ደቂቃዎች ነው የጸሐይ ብርሃን የማገኘው፤ ይሄ እንዲስተካከልልኝ ፍርድ ቤቱን እጠይቃለሁ›› ሲል ያመለከተ ሲሆን፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል በበኩሉ፣ ‹‹ቤተሰቦቼን ያየኋቸው ዛሬ ችሎት ስመጣ ከርቀት ነው፤ ቤተሰቦቼን እንዳይ ይፈቀድልኝ›› በማለት እያነባ ጠይቋል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ደግሞ በጠበቃው በኩል ያለውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ አሰምቷል፡፡ ጠበቃው አቶ አምሃ መኮንን ለስድስት ቀናት ማዕከላዊ ደንበኛቸውን ለማነጋገር ቢመላለሱም ከበር ላይ እንዲመለሱ በመደረጋቸው ከደንበኛቸው ጋር ሳይነጋገሩ ፍርድ ቤት መቅረባቸው አግባብ አለመሆኑንና ድርጊቱ ህገ-መንግስቱን የሚጣረስ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
‹‹ደንበኛየን ያገኘሁት አሁን ነው፡፡ ደንበኛየ የምንፈልገውን ነገር ሳናገኝ ከጠበቃህ ጋር አናገናኝህም ተብሏል፡፡ ይህ በህገ-መንግስቱ የተሰጠውን መብት የጣሰ ተግባር ነው፡፡ አሁንም ደንበኛየ፣ ከዚህ በኋላ እኔን ሳያነጋግር ቃሉን ለመስጠት ፈቃደኛ እንዳልሆነ ፍርድ ቤቱ እንዲመዘግብልኝ እፈልጋለሁ›› ሲሉ ጠበቃ አምሃ መኮንን ለፍርድ ቤቱ ገልጸዋል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እስካሁን በቤተሰብም ሆነ በጓደኞቹም እንዳይጠየቅ መከልከሉ የህግ አግባብ የሌለው የመብት ጥሰት ነው ብለዋል ጠበቃ አምሃ፡፡
ጠበቃ አምሃ ፖሊስ ተጨማሪ ጊዜ የጠየቀበት ምክንያት ደንበኛቸው የዋስትና መብቱ ተከብሮለት ሊከናወን እንደሚችል በማስረዳት የዋስትና መብት እንዲከበርለት ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን በሁሉም ላይ ፖሊስ የጠየቀውን የጊዜ ቀጠሮ በመፍቀድ ለየካቲት 11/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተመሳሳይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከሦስት ወራት በላይ በማዕከላዊ በእስር ላይ የሚገኙት በጋሞ ጎፋ አርባምንጭ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች እነ ሉሉ መሰለ እና አየለች አበበ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበው ‹የመጨረሻ› ነው የተባለለትን ተጨማሪ የ28 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment