Sunday 27 July 2014

ነቀዝ የወጋው ሰብልና ሙስና የነገሰበት ሃገር አንድ ናቸው። – Minilik Salsawi (ምንሊክ ሳልሳዊ)

ሕዝብ፤ ሙስና እየነዳ ላመጣው ግፍ ለዋጋ ንረት፣ ለኑሮ ውድነት፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ ተዳርጓል፡፡ ሙስና ከስልጣን ጋር ተጋብቶ እንደ ሸረሪት ድር ተወሳስቧል፡፡
ሙስና በኢትዮጵያ ውስጥ ተስፋፍቶ መንግስታዊ ሽብርተኝነትን አማክሎ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሕዝብ ዋይታ፣ ለቅሶ ለመሆኑ በቅቷል፡፡ ቢሮክራሲው በሙስና ተዘፍቆ ለስራ ሂደቶች ማነቆ ሆኗል፣ የልማት እንቅስቃሴዎች በመንግስት ሹመኞች ሙስና ተሰነካክለዋል፣ ይህ ነው ለማለት በሚያዳግት ደረጃ ሙስናን ታኮ ግለኝነት ተንሰራፍቷል፣ ስግብግብነት፣ አልጠግብ ባይነትና ማህበራዊ ቀውሶች መገለጫዎቻችን ሆነዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ የመንግስት ለውጥን ተከትሎ የኢትዮጵያ እስር ቤቶችን የሚጨናነቁት በደረቅ ወንጀለኞችና በፖለቲካ እስረኞች ከመሆን ይልቅ በሙስና በተጨማለቁ የመንግስት ሹመኞች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ የሃይማኖት መሪዎችና ነጋዴዎች እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡
የመንግስት ሹመኞችና ባለሟሎቹ የሙስናን በሽታውን ወደ ሕዝብ ነዝተውታል፡፡ ነጋዴው ማህበረሰብ እንደወትሮው ወጭ ገቢውን የሚያሰላው ከቀጥተኛ ወጭው ጋር ያተያያዘውን ግዢና ግብር ብቻ አይደለም፡፡ የቀን ጅብ ለሆኑ ሙሰኞች የሚሰጠውን ኮሚሽንና ውጣ ወረዱን ጭምር ነው። ………… ሕዝቡ የኑሮ ውድነት ከበደኝ! የእቃ ዋጋ ንረት አስመረረኝ! ግፍ በዛብኝ! ሸምቶ መቃመስ አቃኝ የሚል ምሬት ሲያሰማ.. ሹመኞች አፍ ለማስያዝንና ለማሸማቀቅ ይሽቀዳደማሉ፡፡ “በገበያ ስርዓት ነው የምንመራው የሚችል ይገዛል፡፡ ያልቻለ አይገዛም” ይባላል፡፡ ገፋ ሲልም “አጭበርባሪ ነጋዴ ስናሳድድ አንገኝም!” የሚል ማበረታቻ አከል መልስ ለሕዝቡ ይሰጣል፡፡
የተረጋጋ የነበረውን የግብይት ስርዓት ያለበቂ መነሻና ጥናት የዋጋ ጣራ በማወጅ፣ ውቅያኖሱን ደብድቦ አሳውን የሚረብሽ ፖሊሲ ይዘረጋል፡፡ አለመረጋጋቱን ታኮ ነጋዴው እጥረትን፣ የጥራት ችግርን፣ ቅሸባን፣ ሚዛን ማጓደልን አይነተኛ የስራውና የትርፉ መሰረት ያደርገዋል፡፡ ሕዝብ፤ ሙስና እየነዳ ላመጣው ግፍ ለዋጋ ንረት፣ ለኑሮ ውድነት፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ ተዳርጓል፡፡
ዛሬ በኢትየጵያ ውስጥ ቁሳዊ ሙስና እጅና እግር አውጥቶ በሕዝብ ሃብት ላይ እየተጫወተ ይገኛል፡፡ ሃምሳም ስልሳም ሚሊዮን ብር እንደ ቀልድ ከመንግስት ካዝና ሲጠፋ መስማትና እነ እገሌና እነ እንቶኔ ተጠርጥረው ስለተያዙ የተዘረፈውን ለማስመለስ ጥረት ላይ ነን ማለት የተለመደ ሆኗል፡፡ ዘራፊው መጀመርያ ወንጀሉን ያምናል፡፡ ቀጥሎ ከዘረፋው ምንዳ ውስጥ ፍርፋሪ ቆንጥሮ በመስጠት ፣ አምስትና አስር ዓመት ይፈረድበታል፡፡ ለአንድ አመት አስር ሚሊዮን ነው! ምን ችግር አለው! ለጥቆም ደግሞ በአመክሮ ወይም በምህረት መፈታት አለ፡፡
እንዲህ እየተደጋገፉና እየተመቻቹ የሚሄዱ የስልጣንና የጥቂት ነጋዴዎች ሙሰኝነት ስር እየሰደደ ባህል ሆኖዋል፤ መስራትና ማጭበርበር ልዩነታቸው እየጠፋ ነው፡፡ በይና አስበይ በአንድ ቦይ እየፈሰሱ ማን ማንን ይገስጻል፡፡ የሕግ ውክልና የተሰጠው ሹመኛና ሙሰኛ ነጋዴ የሙስናው ፍሬ እኩል ተቋዳሽ ከሆኑ ሕግ ማስከበርም ሆነ ማክበር ፈጽሞ ያዳግታል፡፡ሙሰኛ ነጋዴውም ዋጋ ለማናርና ለመቆለል ምክንያትም ሆነ ስጋት የለውም፡፡ በአቦ በስላሴ እያማካኙ ቀን በቀን ዋጋ መቆለል ነው፡፡ ሙስና ከስልጣን ጋር ተጋብቶ እንደ ሸረሪት ድር ተወሳስቧል፡፡ ለማን አቤት ይባላል! ማንስ ያዳምጣል! መፍትሔስ ከወዴት ይገኛል? ማለት ውሎ አድሮ ቀመሩ “ሙስናን ማጋለጥ ለመላላጥ” ወደ ሚል ከባድ ፍርሃት እንዳይለወጥ በቅጡ ማሰብ የግድ የሚልበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ #ምንሊክሳልሳዊ

No comments:

Post a Comment