Wednesday 8 October 2014

የጥይት ሩምታ በሰንደቅዓላማችን ላይ …. ጥጋቡ መረን ለቀቀ።

ከሥርጉተ ሥላሴ 10.10.2014 /ሲዊዘርላንድ – ዙሪክ/

“ያልወለድኩት ቢለኝ ባባ አፌን አለኝ ዳባ – ዳባ”
እኔ አይደለሁም ዘመኑን በተደሞና በአርምሞ እንዲሁም በፅሞና ሲከታተል ባጅቶ – የከረመው፤ እሰኪበቃው ድረስ በወያኔ 40 ዓመት ሙሉ በቋሳና በቁርሾ የተቀጠቀጠው የኢትዮጵያ ሰንድቅአላማ ነው በመንፈሱ  – የተቃኘው። ለመሆኑ ዬት የሚያውቀውን ሰንድቅዓላማ ነው እንዲህ ወያኔ የሚዘባነነው?! በዚህ ሰንደቅዓላማ ተከብራና ታፍራ የኖረች ሀገር አታስፈልገኝም፣ ገዝታኛለች በማለት አይደለም ትግራይን ከኢትዮጵያ ነጥሎ “የታላቋን ትግራይ” ህልም ለማሳካት እርጥብ ጌሾውን በቂም ምቸት ጠንስሶ ሲዳከር የኖረው። ቀድሞ ነገር በወያኔ ሃርነት ትግራይ ማዕቀፍ ውስጥ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የተፋቀ ነው። ከዚህ መንፈስ ሳትወጡ በጥልቀት መርምሩት …. በሌለ – ባልነበረ –  በአመለ መንፈስ የበቀለ የባዕድ ህልም ተጓዥ በምን ስሌት ነው ዛሬ አጃቢዎቹ ተቆርቋሪነቱን የሚያንኳኩለት ወይንም የሚያንኮሻኩሹለት? …. በዚህ ብሄራዊ ሰንድቅዓላማ ዙሪያ መንፈሱ የወያኔ ሃርነት ትግራይ ኖሮ በፍጹም አያውቅም? መቼ – በዬትኛው ዘመንስ? እስኪ ጫካ እያለ የኢትዮጵያ ሰንድቅአላማ ንጹህ ምስሉን፣ ገጹን በወያኔ ሃርነት ጉባኤዎች ላይ ዬት ላይ ተከብሮ ታደመ? – እንዲሳተፍስ በዬትኛው የወያኔ ሃርነት ጉባኤ ላይ ተፈቀደለት? ምን ያህል ነፃነት ተሰጠው? ይህ እኮ ተፈጥሮው ያልተነነ የዕውነት መሰረተ – ጉልት ነው። ወያኔ በለስ ቀንቶት ከጫካ ወደ ከተማ ሲገባ ለምስል አንድ ቦታ ላይ የኢትዮጵያ ሰንደቅአላማ ያያዘ ሰራዊት ሆነ መሪ አይታችኋልን?! ፈጽሞ አኮ በኢትዮጵያዊነት ሙጣጭ መንፈስ በሌለው ጭድ ግንዛቤ እኮ ነው ሀገር እንዲህ እዬታመሰ ያለው። ወያኔ ከኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ ውጪ የነበረ፣ ያለ – ወደፊትም የሚኖር መሆኑን እውነትን የመቀበል አቅማችን ጋር እባካችሁ ወገኖቼ እንነጋገር። የእኔ ያልሆነው የእኔ ሊሆን ከቶ አይችልም። ለዚህ ነው ከወያኔ አስተምኽሮ የመነሳትን አስፈላጊነት በአጽህኖት ሳልታክት የማሳስበው። ውዶቼ – የኔዎቹ ከዚህ ከተነሳችሁ መንገዱ ቀላል ነው ….
ethiopian-human-rights-activits
የእናት ኢትዮጵያ ያ ወ/ሮ ሞንዳላ ሙሉ ቅርፆዋ እኮ ለወያኔ በሽታው ነው የነበረው። በመንፈስና በአካሏ ተበትና አቅመ ቢስ ስትሆንለት የተነሳበትን ቁርሾ አሳካለሁ ብሎ አይደል ዘመን ይቅር የማይለውን ዘር አምካኝ ድርጅት ወያኔ ሃርነት ትግራይን የተከለው። አረሙ ወያኔ በተጠመጠመ ትብትብ ተብትቦ ነገር እያፈላ ዛሬ ያለችበትን የሞትና የህይወት ግብግብ አና ብሎ ፈጠረ። ተሳክቶለት ሁሉን የመያዝ ዕድሉን አግኝቶ እንኳን ለሰከንድ ሳይዘናጋ ዘነዘናዋን አስቀርቶ እዬገዘገዛት ይገኛል። ሰንደቅዓላማው መቼ ተፈጥረ ብሎ እንደዘገበው ተመልከቱት … “የተፈጠረበት ዓመት ሰንድቅዓላማው በግዕዙ የተጻፈው ቀን ሲተረጎም “ጥር 28 ቀን 1988 ዓም.” ምን? “የተፈጠረበት ዓመት” ታሪክን፤ ትውፊትን – የፈሰሰ ደምን፣ የተከሰከሰን አጥንት ሁሉ ዋጋ አልባ አደረገው። በቁሙ ገድሎ የሚቀብር ዝክንትል ህልም። ለዚህ የላሸቀ ብክነት ነው ፋሽኮው ቀለብ የሚሰፈርለት ሲጮህ የምታዳምጡት ….
http://am.wikipedia.org/wiki/%E1%8B%A8%E1
የኔዎቹ ውዶቼ – ማናቸውም አንጡራ የሃብት ዘረፋው ደግሞ የመንፈሱንም ጨምሮ ለዬትኛው ተልዕኮ ማስፈጻሚያ እንደሚውል “ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ነው።” ጡጦ የሚጠባ ልጅ እኮ አይደለም የኢትዮጵያ ህዝብ። …. እራሱ ብክሉ መንፈስ ከዚህ አጥፊ ድርጅት አፈነገጥኩ የሚለው ጥንስስ ድርጅት ሁሉ ከዚህ አዟሪት የመውጣት አቅም የለውም። …. ሽባ ነው። ይህ ማለት ጥላቻው ሥር ሰደድ መርህ መሆኑን ማመሳክር ይቻላል። እሩቅ ሳይኬድ ይህችን ነጠላ አምክንዮ ይዛችሁ ብትፈትሿት።
እ.ኤ.አ ጥቅምት 5.ቀን 2014 እዚህ ሲዊዘርላንድ ዙሪክ በብራዚል ቆንሲላ ጽ/ቤት ብራዚላውያን በሀገራዊው ምርጫ ሲሳተፉ መዋላቸውን ቴሌ ዙሪ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ሲዘግብ አዳመጥኩኝ። ሰልፉንም አዬሁኝ። ህሊና ያለው፤ ባለቤትነት የሚሰማው፤ የህዝብን ድምጽ የማይፈራ፤ ዬህዝብ ድምጽ አስፈላጊነት የመተርጎም አቅም የተሰጠው፤ እንዲሁም ዘመኑ ለሰው ልጆች የለገሰውን የመብት ነፃነት ያልነፈገ ተግባር እንዲህ ባደላቸው ሀገሮች ይፈጸማል። የሌሎች ሀገር ዜጎች ተሰደውም ሁነኛ አላቸው፤ እረኛ አላቸው፤ ባሊህ ባይ አላቸው – ።
ብራዚላውያን እዚህ ሲውዘርላንድ ላይ ምርጫው ላይ እንዲሳተፉ በክብር ተጠሩ፤ የቻሉት በቦታው ተገኝተው ሲመርጡ ዋሉ። አንዲት ቃለ ምልልስ የተደረገላቸው ወ/ሮ ሲገልጹ እንደሰማሁት ሶስት ሰአት እንደጠበቁ አዳምጫለሁ። ማለት በርካታ ብራዚላውያን ሙሉ ቀን ድምጻቸውን ሲሰጡ እንደዋሉ ተረድቻለሁ። አሁን ወደ እኛ የእንሰሳ አስተዳደር ስንመጣ፤ አይደለም ውጪ የሚገኘው ወገን በሀገሩ ጉዳይ እኩል መሳተፍ እንዲችል መብቱን በሚያረጋግጡ ማናቸው ተሰትፎዎች ተከብሮ መጠራቱ ቀርቶ፤ በሰላም ጥያቄ ሊያቀርብ የሚሄደውን ዜጋ በጽሞና በማዳመጥ ለቀጣዩ አካል ማስተላለፍ ሲገባ በባሩድ ሩምታ ዜግነት ከነአርማው ሲደበደብ አዬን። ከዚህ ሲዊዝ የተፈጸመው የሰው ልጆች የማይገሰስ መብት ተግባራዊነት ለብራዚላውያን፤ በአሜሪካ ደግሞ ኢትዮጵውያን ላይ የደረሰው በቋሳ የጨቀዬ ግፍና በደል ባልተራራቀ ሰሞናት የተከወነው ትዕይንት ምን ያህል የሰብዕዊ መብት ረገጣ ከሀገር አልፎ የዜጎችን ጉዳይ ይወክላል በተባለው ቆንጽላ ጽ/ቤት እንደ ተፈጸመ የሚያረጋግጥ የሀቅ ማህተም ነው። ለነገሩ ባለፉት ወራቶች አሜሪካን ሀገር ተካሂዶ በነበረው የአንባገነን አፍሪካውያን ዬመሪዎች ጉባኤ የህዝብን ሮሮ ያላደመጠው አካል፤ አሁን በዓይኑ፣ በብሌኑ አይቶ ይፈርድ ዘንድ የሰማዩ ዳኛ የላከው የምፅዓት ቀን ደወል ነው። ኢትዮጵያ አምላክ አላት። – አቅሟ – ኃይሏ  – መመኪያዋ  – መጠጊያዋ ፈጣሪያዋ ነውና።
በሌላ በኩል ውጭ ያለነው ተዘለን እንኳን፤ ሀገር ቤት ያለው ዜጋ በትክክል ለውሳኔው ድምጹን በነፃነት መስጠት ይችላል ወይ ለሚለው በስማ በለው ሳይሆን በ97 የተከወነው ጽልመታዊ አንበገነናዊ ድርጊት ምስክር ነው። የጠቆረው ታሪካችንም አካል ነው። ከአራት አመት በኋላም የአደራ አርበኛው አቶ አንዷለም አራጌ እስር ጨምሮ ከዚህው ስጋት የመነጨ ነበር። ለቀጣዩም ምርጫ ቁርሾን ከዝኖ ገና ከመምጣቱ አስቀድሞ እነ አቶ ሃብታሙ አያሌው፤ አቶ ሺዋስ አሰፋ፤ አቶ ዳንኤል ሺበሺና ጋዜጠኛ አብርሃም ደስታ ሰለባ የሆኑበት ምክንያት ይሄው ነው። ያደላቸው ደግሞ በተሰደዱበት ሀገር መብታቸው ተከብሮ በነፃነት ለወደዱት ድምጽ ሲሰጡ አዬን። ብራዚላውያን እርቀው ቢኖሩም መንግሥታቸው የሚያስባቸው መሆኑ፤ በራሱ በሚኖሩበት ሀገርም ተከብረው እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል። አንተ ላጣህ ሌላው ያገልሃል፣ ያቀልሃል ጉዳዩም አይደለም፤ “ባለቤት ያቃለለውን አሞሌ፤ ባለ ዕዳ አይቀበለውም” እንዲሉ። አንተ ለኖረህ ደግሞ ሌላው ይንከባከበሃል – ያሽቃብጥልሃል – ያሸከሽክልሃል። እኛ ኢትዮጵውያን ግን የሁለት ሀገር ስደተኞች ነን። እረኛ አልባ … ምንዱባን …..
አልቀረለትም – ሰንድቅአላማችንም የመከራው ዘመን ታዳሚ ነውና በታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ሲተኮስበት ታዬ – በባዕድ መሬት። ዜጎችም የነፃነት ጥያቄ ባቀረቡ ተመሳሳይ ዕጣ ገጠማቸው። እርግጥ ነው የጫካው አራዊት ወያኔ በጥርሱ ይዞ በጠላትነት ከፈረጃቸው ዬኢትዮጵያዊነት መግለጫዎች ታላቁ ሰንድቅአላማች ነው። ወያኔ ጫካ በነበረበት ጊዜ ሲሰኘው ሲያቀጥለው፤ ሲያሻው የአሞሌ መቋጠሪያ ሲያደርገው፤ ሲለው ደግሞ የእግሩ ገንባሌ አድርጎ ሳይሰቀጥጠው – ሲጠቀጥቀው፤ ከዚህም ባለፈ ሳይፈሩ፣ ሳያፍሩ በድፍረት ትዕቢተኛው የወያኔ መሥራች መሪው ሄሮድስ መለስ ዜናዊ በአደባባይ “ጨርቅ” እያሉ መሳለቃቸው የጨለማው ታሪካቸው ክፍለ አካል ሆኖ፤ ዛሬ ደግሞ በሌለ ልብጥ አርቲፊሻል መንጣጣት … አንገት – የለሽነት።
ወያኔ ቀድሞውን የተነሳበት ኢትዮጵያዊነትና ኢትዮጵያን ማጥፋት በመሆኑ በዚህ ዙሪያ ያሉ ተቋማትን ካላ ምህረት ነው በተከታታይ ከትክቶና ቀጥቶ ለማምከን የሚታገለው። ዛሬም ቢሆን እዬነጠሉ የእሳት እራት የሆኑ አርበኞቻችን በሰንድቅአላማቸው ላይ የማያወላውል ቁርጠኛ አቋም ያላቸው፤ የማይደራደሩም በመሆናቸው ብቻ ነው።
እዚህው ዘሃበሻ ላይ 8ጊዜ የኢትዮጵያ ሰንድቅዓላማችን እንደተቀያዬር የሚገልጽ ጹሑፍ አንብቤያለሁ። ምን ለማለት እንደሆነ ባይገባኝም፤ አስፈላጊነቱም ለአሁን ጊዜ ምን ያህል እንደሆነ ባይረዳኝም፤ ምን አልባትም ለነገ የጠራ አቋም እንዲያዝ ታስቦበት ሊሆን ስለሚችል ሃቁን ማንጠር ያስፈልጋል። ከወያኔ በፊት በነበረው ጊዜ ሰንድቅዓላማችን ላይ ሌላ የመንግሥት ታካይ ውክል ፍላጎት ቢኖርበትም ሰንድቅዓላማችን በአዋጅ አልታሰረም፤ አልተረሸነም፤ ማዕቀብ አልተጣለበትም፤ አልተቃለለም፤ አልተንቋሸሸም፤ በክፉ ዓይን አልታዬም፤ አልተገላመጠም፤ በወንጀለኝነት ተጠያቂም አልነበረም – አልተገፋም እንዲያውም የሚያበረታታ ተግባር ነበር ሲከወን የኖረው። ክብሩ – ማዕረጉ –  ሙላቱ – ልክ አልነበረውም። ዋቢ ላለው ሀገራዊ ተልዕኮ እራሱ መሪ – ተመራጭ  – አደራጅ – አስተናባሪ – ግንባር ቀደም እንዲሆን ያልታሰረ ንጹህ ነፃነት ነበረው በግርማና በሞገስ ነበር።
በምልሰት የነበረውን ተደማጭነት ሆነ ተቀባይነት ሲገመገም፤ በዬጊዜው ማህሉ ላይ ተጨመረበት የሚበልለት ሰንደቅዓላማ የመንግሥት አካላት በቢሮቸው ከሚያስቀምጡት በስተቀር በዬትኛውም ቦታና ጊዜ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ለመላ ኢትዮጵያ ህዝብ የእትብት ውስጥነት መለያ ረቂቅ መንፈስ የነበረው፤ ለዜጎች የማንነታቸው መግለጫ፣ የሐሤታቸው ማፍኪያ፣ የሃዘናቸው ማስታገሻ – ማጽናኛ፤ እንዲሁም የዕምነታቸው – የአውዳማታቸው ሆነ የባህላቸው አባዎራቸው፤ ዓዕምዳቸው፣ አንጎላቸውና አንገታቸው የአድህኖ ምስላቸው ነበር – የነበረው። ዜጎች የዳር ደንበራቸው ልዩ የክብር ጌጥ አድርገው አምልከውትም ኖረዋል። ይህን በማድረጋቸው ደግሞ አይታሰሩም፤ አይንገላቱም፤ ወይንም አይሰደዱም ወይንም ሰው ሳያይ ሰንደቅዓላማቸውን እንደለበሱ በቂም በቀል አይገደሉም። ሆኖም ተደርጎም አያውቅም። ስለዚህ የዛሬው የበቀል ቅጥቀጣ ምንጩ አንድ ነው ባንዳነት ነው። ኢትዮጵያ በነፃነት ተከብራ መኖሯ፤ ሉዕላዊነቷ ተደንቆ – ደምቆ መኖሩ፤ የአፍሪካ ቀንድ ማዕከል መሆኗ የጎረበጠው የጫካ አራዊት ትናንትም ዛሬም – ነገም ለሰንደቅዓላማችን ጠላትነቱን በዬአጋጣሚው እዬገለጸ ነው።
በምንም ዓይነት መስፈርት በዐጤው ጊዜም ሆነ በዘመን ደረግ የነበረው የሰንድቅዓላማ የመንግሥት የጥበቃና የእንክብካቤ ደረጃ ከባንዳው ወያኔ ጋር ለማነፃፀሪ ማቅረብ በሥጋ የሌለች አንስት ነፍሰጡር መሆን ትችላለች ብሎ የማመን ያህል ነው ለሃቁ የሚርቀው – ለዬትኛውም የማነፃፀሪያው ሆነ ዬማካካሻ ድርድር። … በህግ አምላክ! እንዲህ ከተቀረቀረ መንፈስ ጋር ዬቀደምት ግርማ ሞገስ ከዚህ ጉማማ ዘመን ጋር አይነካካ። ከዚህ ባለፈ እማማ አፍሪካን የነፃነት ወተት አጥትቶ እራሷን ያስቻለ አንቱ ነው – የኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ – የቅኔ ሊቃውንቱ። ድንበር አልቦሽ ተወዳጅና ተናፋቂ የበኽረ ነፃነት የጥቁር ዕንቁ አንድምታ ነው ሰንደቅዓላማችን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ።
ይህ ለዚህ ንቁ ትውልድ በእጁ ያለ፤ ክፉና ደግ የሚሰማበት፤ በጎሪጥ የሚታይበት፤ ብሄርተኛ እዬተባለ የሚገለልበትና የሚቀጠቀጥበት በመሆኑ ለቀባሪው አረዱት ይሆናል። ነገ ወያኔ ሊያደርገው የሚችል ቀጣይ ነገር ይኖራል። አንድነታችን እንዲሸረሽር ታስቦ በተዘጋጀው የመርዝ ስሌት ብቀላ ምስል ላይ በህዝብ ድምጽ በጉልበት እንዲጸድቅ ሊያደርገው ይችላል። ማዋጋት – ዕዳ ትቶ ማለፍ የወያኔ ህልሙ ነውና። ባህሪውም ይኼው ነው። ዜጎችን ሰላም መንሳት – ማወክ – መወጠር – መንፈስን ማባካንና ማፈናቀል። ነገር ግን ….  ኢትዮጵውያን ትናንት የሞቱለት ዛሬም የሚሞቱለት ሰንደቅዓላማ ግን መቼውንም ህያው ይሆናል። ይኼው ታሪክ እራሱን ደገመና ደረታቸውን ለጠላት ባሩድ የሰጡ ጀግኖች የወያኔን ምልክት በጀግንነት ከቦታው አወረዱትም። “ … ወደ ኤምባሲው ገብተው የነበሩት ኢትዮጵያውያንም በአሁን ወቅት የኢህአዴግ  መንግስት የሚጠቀምበትን ባለኮከብ ሰንደቅዓላማ በማውረድ የቀድሞውን ታሪካዊ የኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ ለተወሰነ ጊዜ ሰቅለው ከግቢ እስኪወጡ ማውለብለባቸው በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ጠቁመዋል፡፡ https://addismedia.wordpress.com/tag/usa-ethiopian-embassy-tplf-eprdf/” ነገም ይቀጥላል። የናፈቃቸው፤ ዓይናቸው የራበው በተሰደዱበት ሀገርም ሰንደቅአላማችው ከንክብሩ ሲውለበለብ ማዬት ነበርና በጀግንነት ፈጽመው ቆይታቸውን ቀለማም አደረጉት – የዘመናት አብነታዊ ተቋማት። ኑሩልን – ጀግኖቻችን – ኩራቶቻችን።
ይህን በደማችን ውስጥ የሚንቀለቀለውን የብሄራዊ ስሜት መግለጫ ወያኔ ማምከን ፈጽሞ አይችልም። ደምና ሥጋ ነው ለእኛ ሰንደቅዓላማችን። መንገድ ላይ ፊት ለፊት ሰንደቃችን አጊጠንበት ከወያኔ ተላጣፊዎች ጋር ስንገናኝ እንዴት በመንፈሳቸው ላይ ቤንዚን እንደሚያርከፈክፍ ሰንደቅአላማችን የሚያውቀው – ያውቀዋል። የወያኔ ጀሌ መንፈስ ሰንደቃችን ለብሰን ሲዩ የተለበለበ ግንድ ነው የሚመስሉት። አሁንም ይሄን አጠናክሮ መቀጠል ያስፈልጋል። የተሰወረው ጥቃት አውጪ ቦንብ ነውና። ነገ አዲሱ ትውልድ መታጋል ያለበት ምንም ያልተለጠፈበት ዋጋው ከፍና ዝቅ የማይል ዬኢትዮጵያ ሰንድቅዓላማ ብቻ ድምጽና ነፍሱ መሆኑን በድርጊት ለጠላቱ ማሳወቅ አለበት። የትኛውም ዓይነት መንግሥትና ሥርዓት ይፈጠር ከእንግዲህ ቢያንስ የሰንድቅዓላማችን ህልውና ቋሚ መሆን መቻል አለበት። ከዚህ ለሚወጣ ማናቸውም የሀገሬ ጉዳይ ያገባኛል የሚል ኃይል ቢሆንም ድምጽን መንፈግ ግዴታችን መሆን ይገባዋል። ብሄራዊ ዓርማችን – ምልክታችን – የወልዮሽ ሃይማኖታችን ንጹሑ አረንጓዴ ቢጫ ቀዩ ብቻ ይሆናል።
ለዚህ ደግሞ አዲሱ ትውልድ ጀምሮታል – ይቀጥላል። ደግሞ ወግ አይቀርም “ሰንድቅዓላማችን ተደፈረ” ተባለ። የት የሚያውቀውን ነው ወያኔ …. ያ … ጨርቅ እያለ ያላገጠበት፤ ያባጫለው፤ ገድለን ቀብረነዋል እያለ የቅራራበት እኮ ነው። ነገር ግን  ማንነት የትም ቦታ በዬትኛውም ሁኔታ ደም ነውና ጎልቶ ጎልብቶ ገኖ ደምቆ – ይጎመራል።
ትናንት የተፈጠሩ፤ ውጪ ሀገርም ተወልደው ያደጉ የተስፋ ዕንቡጦች ዛሬ ሰንድቅአላማቸው የትኛው እንደሆነ ለይተው በሚገባ ያውቁታል። እንዲህ በተመሰጠ – በድንግልና ጥልቅ መንፈስ እንሆ የነገ የተስፋ ልዕልት፤ የሰባዕዊ መብት ተሟጋቿ፤ የፓን አፍሪካኒስት ሩኽ መንፈስ ያልተለያት እመ – ትጉኋን ሳምራዊት ተሰማ ደግና ገዱን መንገድ ሐዋርያ ሆና እዬሰበከች ነው። ድንግልዬ ትጠብቅልን። ውስጧን አንብቡት የኔዎቹ። ሰንደቋ ታቦቷ ነው – ለትውፊት።
ቀደምት አርበኞች እለሞቱም አሉ። ደጎቹ – ደግን ይኼው ተክተዋል። ዓርማቸውን ከፍ አድርጋ አክብራ የምታስከብር አልማዝ እነሆ ሸልሞናል – አምላካችን። ተመስገን! እልፍ ናቸው ዬሰንደቅዐላማቸው ፍቅር ስፍስፍ ዬሚያደርጋቸው – ቀንበጦቻችን። የኢትዮጵያ ሰንደቅ መንፈስ ነው።  መንፈስ አይሸመትም  – አይበደሩትም። አይታመም – ሞትም ድርሽ አይልበትም። የማይለወጥ ቋሚ የደም ማገር ነውና።
የማከብራችሁ ወገኖቼ – በሀገረ አሜሪካ ሰንደቅዓላማችን እንደዛ ባሩድ ሲነጣጠርበት ማዬቱ እራሱ ይሰቅጥጣል። መታሰቡ እራሱ ያንቀጠቅጣል። ዜጎችን ለመግደል ብቻ ታስቦ አልነበረም የተተኮሰው። ሰንደቅዐላማችን ለመግደል – መንፈሱን ለማቁሰል – ቅስሙን በዓለም አደባባይ ለመስበር – ክብሩን ለማዋረድም ታስቦ ነበር። ግን ፍርዱ የሰው ሳይሆን የሰማይ ሆነና ያላመጠውን ሳይውጥ ወንጀል ፈፃሚው ተጠቅልሎ – ተቀጣበት። የቃልኪዳን ውል እንዲህ ይፈርዳል። ሌላም ይኖራል። ዬሰንድቅዓላማ ስጦታው በሰውኛ ፍቺ አይደፈርም – ከቶውንም። ለ1988 ተፈጠረ ለተባለ ልብድ ምስል አለንለት ብሎ አደባባይ መውጣትም – ዝልቦነት ነው። ማፈር- መሸማቀቅ ሲጋባ እንዲህ ጥጋብን አደባባይ ማውጣት የመጨረሻው እራስን ዬማነቅ ትዕይንት ይሆን – ይሆን? የእኔ ውዶች ፍቱት ወይ ተርጉሙት – አቅም ያላችሁ።
ክብረቶቼ ስንብት እናድርግ፤ የሃሳብ ልዩነትን በሰለጠነ መልክ ማስተናገድ ማለፊያ ነው። ስለሆነም በሁለቱም ወገን የታዬው ትክክል ነው የሚሉ ወገኖች ይኖራሉ። ይህ በሃሳብ ላይ አይደለም። በማንነት ላይ ነበር። ነገር ግን ቅኖች ወገኖቼ ልብ ሊሉት የሚገባው አብይ ጉዳይ በማንነት ላይ ውይይትም ድርድርም የለም። ለማንነት አጀንዳ አይያዝለትም። ስለዚህ በነፃነት ሀገር ሃሳብን በሃሳብ የማታገል መርሁ እንዲህ ተግባራዊ ሲሆን ማዬት መልካም ሆኖ ሳለ፤ በሰንደቅአላማችን የጥይት ሩምታ ጉዳይ ግን ቁርጥ ያለ አቋምና ውሳኔ፤ እንዲሁም የጠራ መስመርም መከተል አለብን። እኛ ብቻ እኮነን በቀደምትነት የሰው ልጅ መፈጠሪያ ሆነን የሚያስማማ ብሄራዊ መዝሙር፣ ሰንድቅአላማና ህገ መንግሥት በዓለም የሌለን ህዝቦች። ይህን መራራ ዘመን ለመዋጀት አለን የሚሉ ድርጅቶች ሁሉ የፍላጎታቸው አስኳል ሊያደርጉት ይገባል – አምክንዮ። በተረፈ የፊታችን ሃሙስ Radio Tsegaye 09.10.2014 የተለመደ ዝግጅት ይኖረዋል። የቻላችሁ እ.ኤ.አ ሰዓት አቆጣጠር ከ15 እስከ 16 ሰዓት ላይ፤ ያልቻላችሁ ደግሞ አርኬቡ ላይ ታገኙታለችሁ ማድመጥ ትችላላሁ – ፈቃዳችሁ ከሆነ። ደህና ሁኑልኝ – ኑሩልኝ።
ኢትዮጵያዊነት ፈተናን አሸንፎ የተፈጠረ ሚስጢር!
እግዚአብሄር ይስጥልኝ።

No comments:

Post a Comment