Sunday 5 October 2014

ዶ/ር ጳውሎስ አለፈ፤ የቀብር ስነ ስርዓቱ የፊታችን ቅዳሜ በቦስተን የሚፈጸም መሆኑ ታውቋል!! – ከአርአያ ተስፋማርያም

ዶ/ር ጳውሎስ አለፈ፤ የቀብር ስነ ስርዓቱ የፊታችን ቅዳሜ በቦስተን የሚፈጸም መሆኑ ታውቋል!! የቀብሩን ዝርዝር መረጃ እናዳገኘን እናስታውቃለን።
ደግነትን፣ ለአገርና ወገን ተቆርቋሪነትን፣ በሙያው ለሚሳቃዩ ወገኖች ነፃ የህክምና እርዳታ መስጠትን፣ አክብሮት የተሞላበት ትህትናና የሰዎችን ሃሳብ በዝምታና ትእግስት የማዳመጥን፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮችን በበሳል ሁኔታ የማስረዳትና የመተንተንን፣ ለኢትዮጵያና ለዜጐቿ ዘወትር በማሰብ ከተገፉና በጭቆና ስር ለሚማቅቁ ወገኖች በገንዘብና በሙያው ፍፁም ተቆርቋሪነትን በተግባር ጭምር ማረጋገጥን…. ወዘተ የተለየ ድንቅና ውድ ስብዕና የነበረውን ዶ/ር ጳውሎስ ከእንግዲህ ላናገኘው ተለይቶን ሄደ። የዶ/ር ጳውሎስ ህልፈት ብዙዎችን ጥልቅ ሃዘንና ድንጋጤ ውስጥ ከቷቸዋል። በህይወት ዘመኔ ከተዋወቅኳቸውና ልዩ ስብእና ከተላበሱ እጅግ መልካም ሰዎች የተለየ የክብር ስፍራ የምሰጠው ዶ/ር ጳውሎስ ምን እንደምል ቸገረኝ! ..የ30 አመት የጳውሎስ ወዳጅና የትግል አጋር የሆነው አቶ ኢሳይያስ አሁን ከመሸ ሳገኘው በሃዘን ኩርምት ብሎ ነበር።
ኢሳይያስ በሃዘን ስሜት « ጳውሎስ ለራሱ ሳይኖር ስለሌሎች ኖሮ ያለፈ የጥንካሬና የመልካምነት ተምሳሌት ነው! የአገሩና የወገኑ ነገር እረፍት የሚነሳው የእውነት ሰው ነበር!..» አንገቱን እንዳቀረቀ ዝም አለ። ከዛ በላይ መናገር አልቻለም።.. በዲሲ የተለያዩ ሃበሾች ተመሳሳይ የሃዘን ድባብ ውስጥ ናቸው። በትላንትናው እለት ከዚህ አለም በሞት የተለየው ዶ/ር ጳውሎስ የቀብር ስነስርዓት የፊታችን ቅዳሜ በቦስተን የሚፈፀም ሲሆን በእለቱ ለመገኘት በርካቶች ከዲሲ ለመሄድ ተዘጋጅተዋል።
ዶ/ር ጳውሎስ ከዲሲ ወደ ቦስተን ያቀናው በቁም እስር ለሚገኘው ለልጁ ወጣት ሮቤል ሲል ነበር። ..ግን..ግን ለምንድነው መልካም ሰዎች በዚህ ምድር የማይበረክቱት!?.. ጳውሎስን የመሰለና ገና ረጅም የህይወት እቅድ (ለአገሩና ወገኑ) የነበረው ታላቅ ሰው ማጣት ያንገበግባል!! ..ፈጣሪ ሆይ ለምን!?

No comments:

Post a Comment